ምድራችን ካስተናገደቻቸው
አስከፊ ገጽታ ካላቸው ጦርነቶች መካከል አንዱ በተለያዩ ዘመናት "በክርስቲያኖች" የተመራውና ብዙ ሚሊዮኖችን ለህልፈት
የዳረገው የመስቀል ጦረኞች ጦርነት ነው፡፡ ጦርነቱን ጳጳሳት በመባረክ፣ካህናት ጸሎት በማድረግ ይራዱ እንደነበርም ተዘግቧል፡፡ሰውን
ወዳዱ ጌታ ኢየሱስ የፍጡር ደም መፍሰሱ እንዲያባራ ሰላምና ፍቅር እንዲሰፍን በመስቀሉ ደሙን አፍስሶ ሲያድነን አመጸኛ ክርስቲያኖች
ግን የሰላም ስሙንና አርማውን አንግበው ምድሪቱን በግፍ ደም አጥለቀለቋት፡፡
ክርስቶስ
ኢየሱስ ፣መድኃኒቱ ጌታ "ስለእኛ የተረገመ ሆኖ ከህግ እርግማን ሊዋጀን" ፤ ከኃጢአታችንም ሁሉ ሊያነጻን ፤የእኛን
በኃጢአት መረገም አርቆ የእርሱን ጽድቅና ቅድስና እንዲሁ ያለዋጋ ሊሰጠንና "የመንፈስን ተስፋ በእምነት እንድንቀበል"
እርሱ እንደህጉ የተረገመ ሆኖ በመስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡(ገላ.3÷14) እርሱ የተሰቀለው ህይወት እንዲሆንልንና እንዲበዛልን ፣መዳናችንም
እውን ሆኖ ከኃጢአት ባርነት ነጻ እንድንወጣ ነው፡፡
እኛን ኃጢአተኞችን ከኃጢአት ባርነትና ከህግ መርገም ነጻ ለማውጣትና ለማዳን
የተከፈለው ተካካይ የሌለው ዋጋ የመስቀሉ ቃል የተባለ የክርስቶስ ሞትና (ገላ.3÷13) የከበረ ደሙ ነው፡፡(1ጴጥ.1÷19) እርሱ
በመስቀል ካልተሰቀለ ደሙንም ለስርየት ካላፈሰሰ በቀር እኛ ወደእርሱ፣ በሰማያት ወዳለአባቱም መቅረብ አይሆንልንም፡፡(ዮሐ.12÷32፤
ኤፌ.2÷13)፡፡
ከምድር እስከሰማይ የተዘረጋው ያ እውነተኛ የያዕቆብ መሰላል ክርስቶስ(ዮሐ.1÷52)
በመስቀል ላይ በዋለ ጊዜ እግዚአብሔርና ሰውን የለየው የዘመናት የጠብ ግድግዳ ፈርሶ ሰውና ሰው፣ ሰውና እግዚአብሔር ፍጹም ታርቀው
አንድ ሆነዋል፡፡የነበረብንም የዕዳ ጽህፈትና በደል በተትረፈረፈው በመስቀሉ የደም ዋጋ ተደምስሶልናል፡፡(ቆላ.1÷20፤2÷14፤ራዕ.12÷11)