Please read in PDF
3.ሌላው አጽናኝ ወደ እኛ ይመጣ ዘንድ፤
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ መስቀል
ነፍሱን ስለ ሰው ልጆች አሳልፎ ሊሰጥ እጅግ በቀረበበት ሰዓት፣ ደቀ መዛሙርቱ እጅግ ማዘን ጀምረው ነበር፤ ተላልፎ እስከ
ተሰጠባትና መስቀል ላይ እስከ ወጣበት ጊዜ ድረስ መከራው በሙሉ ያነጣጠረው በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ነው። ነቀፌታውም፣
ስድቡም፣ ትችቱም፣ ጥላቻውም፣ መገለሉም፣ መሰደዱም፣ በመጨረሻም በመስቀል ከባድ መከራንም የተቀበለው ጌታችን ኢየሱስ ነው።
ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን መከራው እነርሱንም እንደ ሚያገኛቸው አስቀድሞ አልነገራቸውም፤ ምክንያቱም በእርሱ ሕይወት ሲያልፍና
ሲኾን የነበረውን ኹሉ ሲመለከቱ ነበርና። ከንግግር ይልቅ ሕይወት የማስተማር አቅሙ እጅግ ታላቅ ነውና!
ነገር ግን ወደ ሰማያት ወደ አባቱ ሊሄድ ሰዓቲቱ
እንደ ደረሰች ሲያውቅ፣ “እንዳትሰናከሉ ይህን ተናግሬአችኋለሁ። ከምኵራባቸው ያወጡአችኋል፤ ከዚህ በላይ ደግሞ የሚገድላችሁ ሁሉ
እግዚአብሔርን እንደ ሚያገለግል የሚመስልበት ጊዜ ይመጣል።” (ዮሐ.16፥1-2) በማለት፣ መከራው ለእነርሱም እንደ ማይቀር
ነገራቸው። በጌታችን ኢየሱስ ላይ የወረደው የዓለሙ ኹሉ ጥላቻ በእነርሱም ይፈስሳል፤ የተገለጠ ንቀትም ፊት ለፊት ያገኛቸዋል፤
በዓለሙ ኹሉ ፊት እንደ ጉድፍ ይቆጠራሉ፤ ጌታቸው ባለፈባት የምጥ መንገድ እነርሱም ያልፉ ዘንድ አይቀርላቸውም። የመከራው ጫፍ
ሰዎች እነርሱን ሲጠሉ፣ ሲያሳድዱ፣ ሲገድሉ … ለእግዚአብሔር መሥዋዕትን የማቅረብ ያህል በጭካኔ ያደርጉባቸዋል። በዛሬ ዘመን
ምን እየኾነ ይኾን? ሰዎች የእግዚአብሔር ሰዎች ነን እያሉ፣ በሃይማኖት ሽፋን ሰዎችን ለምን ይገድላሉ? ይጠላሉ? ያሳድዳሉ?
የሰዎችን ስምስ በመረረ ጥላቻ ለምን ያጠፋሉ? …።

