Please read in PDF
ማኅሌታይ ያሬድ የዓቢይ ጾምን ኹሉንም
ሳምንታት ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወትና ትምህርት እንዲኹም ማንነት ጋር በማዛመድ ስያሜ ሰጥቷቸዋል፡፡ ከዚህም የተነሣ ይህ
አሁን ያለንበት ሳምንት ስያሜ ገብር ሔር ይባላል፤ ትርጉሙም መልካም ባርያ ማለት ነው፡፡ የስሙ ትርጉም የተወሰደው ከማቴ.25፥23
ላይ ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ በዚያ ክፍል በመልካምነትና በታማኝነት ስላገለገሉ አገልጋዮች ስለሚሰጠው ታላቅ ሽልማትና ክብር እንዲሁም
ደግሞ፣ ላልታመኑት አገልጋዮች እንዴት ያለ ታላቅ ተግሳጽና ዘለፋ እንዲሁም ፍርድ እንደሚያገኛቸው ያስተማረበት ክፍል ነው፡፡
የተሰጠን መክሊት በአግባቡ መጠቀም እጅግ አስተዋይነት ነው፡፡ መክሊቱ ልዩ
ልዩ ሥጦታን የሚያመለክት ነው፤ ሥጦታዎቹ መንፈሳዊም ኾኑ ሥጋዊ ሥጦታዎች፣ የተፈጥሮ ወይም የመንፈስ ቅዱስ ሥጦታዎች ሊኾኑ ይችላሉ፤
(1ቆሮ.12፥7-11፤ ገላ.5፥22) ራሱ መንፈስ ቅዱስም ለሚያምኑ ኹሉ የተሰጠ ውድና ክቡር ሥጦታ ነው፡፡ ስለዚህም የሁሉ ሥጦታዎቻችን
ምንጭ ራሱ እግዚአብሔር አምላክ እንጂ እኛ አይደለንምና በሥጦታዎቻችን ልንመካ አይገባንም፡፡ ከመጀመርያም የሥጦታ የመሰጠት ምክንያቱ
ለእኛ ሳይኾን ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ነው፤ እኛማ ከፍጥረታችን እኛ የቁጣ ልጆች እንጂ ምንም መልካም ነገር ያልነበረንን ነን፤
(ኤፌ.2፥3)፡፡ ስለዚህ ታማኝነታችንን መግለጥ የሚገባን በተሰጠን መክሊት ልክ ነው፡፡


