Sunday, 26 April 2020

በሕማሙና በትንሣኤው ዙርያ የነበሩ ምስክሮች (ክፍል አምስት)


3. ትንሣኤውን በመመልከት ኹሉን ትቀድማለች፦ ባለፉት ጊዜያት ጌታ መንፈስ ቅዱስ እንዳስተማረን፣ በመግደሎሟ ሴት ኹለት ነጥቦችን አንስተን፤ ሰባት አጋንንት ያወጣላትና እንዲሁም የጌታ ኢየሱስን ሕይወትና ትምህርት ተመልክታ፣ ፍጹም የተከተለችው መኾኑን አንስተናል። ከዚሁ ቀጥለን የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ምስክሮች ስለ ኾነችው ሴት በጥቂቱ እንመለከታለን።


Friday, 24 April 2020

ቅንነት ጥሎ፤ ዘፈን አንጠልጥሎ!

Please read in PDF
    ተኩላው ወደ በጐች ጐረኖ መሰስ ብሎ ሲገባ፣ ዝም ማለት ወይም ባላየ ማለፍ “ተለመደ”፤ የእግዚአብሔርን ምሕረት አስታክኮ፣ ኀጢአትን “ምን አለበት?” እያሉ ማላመድ የለቀቅተኛ ነገረ መለኮታዊያንና በሰልን ባይ አማኝና አገልጋዮች መገለጫ ኾነ፤ ኀጢአትን መጠየፍ አጉል አክራሪነት ተባለ፤ ኀጢአተኝነትን መካድና መቃወም ተቃዋሚነትና ከሳሽነት ተብሎ ተፈረጀ፤ ግብረ ሰዶማዊው አገልጋይ ሲሰብክ፣ “መጀመሪያ ንስሐ ግባ!” ማለት ግብዝነትና ማካበድ ኾነ፤ በተቃራኒው ደግሞ ዘፋኝነት ከመዝሙርነት ሲጣባ መንፈሳዊ ግልጋሎት፣ ኢየሱስን የሚጋርድ ተግባር ትክክል፣ የተሰቀለውን ክርስቶስ የሚሸቅጥ ተግባርና ዐሳብን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ለማድረግ ጥቅሶችን ማስጨነቅ ተወደደ፤ ተኩላውን ከመንጋው ማላመድ “ካውንስል” ተብሎ ተሞገሰ፤ ኢየሱስ ሳይኾን ቡድንና አገልጋይ ነኝ ባይ በሰው ልብ ገነነ፤ ለቀቅተኞች ቤተ ክርስቲያንን ንብ የማር ቀፎን እንደሚከብብ ከበቡአት። 

Wednesday, 22 April 2020

ተነሥቶአል!

Please read in PDF
ይህ ታላቅ ምስክር የተሰጠው ለታላቁ መሲህ ለክርስቶስ ኢየሱስ ብቻ ነው፤ ሞት ብርቱ ሥጋ ለባሽን ኹሉ አሸንፎ ገዝቶአል፤ በጦር ሜዳ ጀግኖች የነበሩትን አርበድብዶ፣ “በውኑ ሞት እንደዚህ መራራ ነውን?” (1ሳሙ. 15፥32) በማስባል፣ በፊቱ አንበርክኮአል። ሞት ያልገዛው ብርቱ፣ ያልሻረው ኃያል፣ ያልጠቀለለው ጎበዝ፣ ያልዋጠው አለቃ፣ ያልሰበረው ጠንካራ … በምድር ላይ ከቶ አልነበረም። ሞት ወደቀውን ዓለም ተከትሎ፣ በሰው ልጆች ኹሉ ነግሦ ኖሮአል፤ “በአንዱም በደል ሞት በአንዱ በኩል” ወደ ሥጋ ለባሹ ዓለም ሰተት ብሎ ገባ፤ (ሮሜ 5፥17) እንዲል።


Friday, 17 April 2020

የሃይማኖት መሪዎች በኢየሱስ ላይ ለምን ተነሣሱ?

Please read in PDF
   በሰሙነ ሕማማት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሥጋ ሞቱ ይዘከራል፤ ስለ ሞቱ የተነገሩ ክፍሎች በብዛት ይነበባሉ፤ ይፈከራሉ፤ ይታተታሉ። በእነዚህ ጊዜያት አብዛኛውም የክርስቲያን ማኅበረ ሰብ “የፍለጋውን ዱካ” ወደ መንፈሳዊ ነገሮች ሲያደርግም ይታያል። መጠጥና ጭፈራ ቤቶች፣ የቁማር፣ የጫት መቃሚያና ሺሻ፣ ጋንጃ መማጊያ ቤቶች ከወትሮው ጊዜ በተለየ፣ ሰዎች ጐራ አይሉባቸውም[ኮቪድ 19 ኮሮና ጭርሱን ጠረቀመልን - እሰይ - ኡፈይ]። በሰሙነ ሕማማት የዘፈን ኮንሰርቶች፣ የመጠጥ ድግሶች ጨርሶ አይታሰቡም፤ ይህ ግን ከሳምንት ያላለፈ ጥንቃቄና መጠበቅ መኾኑን ስናስተውል፣ ነገሩ መንፈሳዊ ሳይኾን የግብዛዊነት ጠባይ መኾኑን እንረዳለን።



“ለይሁዳ ወልዱ ወውሉደ ወልዱ ይደምሰስ!” ለምን አንልም?

Please read in PDF
   በሰሙነ ሕማማት ከምናስተውለው አስደናቂ ነገር አንዱ፣ ይሁዳን የሚረግሙ ሰዎችና አብያተ ክርስቲያናት የመብዛታቸው ጉዳይ ነው። ለክርስቶስ ተላልፎ መሰጠት ይሁዳን ተቀዳሚ ተጠያቂ በማድረግ፣ ይሁዳንና ዘር ማንዘሩን የሚራገሙና የሚኰንኑ፣ የአምልኮ አካላቸውም አድርገው፣ የይሁዳን ኀጢአት ዘክረው፣ በብዙ የሚወቅሱ አያሌ “ክርስቲያኖች” አሉ። ክፋትን መጠየፍ አንድ ነገር ቢኾንም፣ ከእውነት ብዙ መራቅ ግን ግብዝነትን ያጐላል።


Wednesday, 15 April 2020

መሲሑ ሲደነግጥና ሲያጣጥር!

Please read in PDF
   ከኢየሩሳሌም ከተማ በቄድሮን ወንዝ ማዶ በደብረ ዘይት ግርጌ ባለው የአትክልት ስፍራ፣ ጌቴሴማኒ እየተባለ በሚጠራው ስፍራ፣ ሐሙስ ማታ፣ “የናዝሬቱ ኢየሱስ … በተአምራትና በድንቆች በምልክቶችም ከእግዚአብሔር ዘንድ … የተገለጠው ሰው” (ሐዋ. 2፥22)፣ “ሊያዝን ሊተክዝም ጀመር” (ማቴ. 26፥37)። ጌቴሴማኒ መልካሙና መሃሪው ጌታ ኢየሱስ ስቃዩን የጀመረበት ስፍራ ነው፤ ስለ ሰው ልጆች ኀጢአትና በደል፣ እርሱ የምድርና የሰማይ ሐዘንና ትካዜ በእርሱ ላይ ወረደ፤ በዚያም ሌሊት ብቻውን ተሳቀየ።
   

Sunday, 12 April 2020

ጌታ አኹን አድን

ስለ በዛው ጣዕር ስለ ሕፃናት ዋይታ
ስለ አዛውንቱ ስለ እናቶች እንባ
እንደ ቅጠል ረግፎ ቀብር በወረደው

Thursday, 9 April 2020

የ“ዲያቆን” አሸናፊ መኮንን፣ አዲሱ ድርሳነ ማርያም (ክፍል ፪ እና የመጨረሻ)

Please read in PDF

የወንጌሉን ዓላማ በመሳት፣ በአሸናፊ የተተረጐሙ “ትርጓሜያት”


1. የሰርጉ ተቀዳሚ ዓላማ “የእመቤታችንን የድንግል ማርያምን የእምነት ጸሎት ለማብራራት ነው”[1] የሚለው፣ የዮሐንስ ወንጌል ተቃራኒ ዐሳብ ነው። “ዲያቆን” አሸናፊ፣ እመቤታችን የጸለየችው ጸሎት ተራ ጸሎት አይደለም ቢልም፣ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ኹለት ውስጥ ጸሎት መኖሩን አናነብም ወይም ወንጌላዊው ዮሐንስ፣ ቅድስት ማርያም ጸሎትን መጸለይዋን አልጻፈልንም። ይህን ለማለት አስግጎ ወይም ወደ ቃሉ በማሰገባት የተረጐመው ክፍል፣ “የወይን ጠጅም ባለቀ ጊዜ የኢየሱስ እናት፦ የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም አለችው።” የሚለውን አንቀጽ ነው፤ (2፥3)።[2] ጸሎት ነው ከማለት ባለፈ፣ አስደናቂ ልመና፣ የቃና ዘገሊላው ጸሎት፣ የድንግል ጸሎት እያለ ሲያሞጋግሰው እናስተውላለን። ከዚሁ ጋር በተያያዘም ጸሎት ያለውን አንቀጽ፣ “እንደ ፈቃዱም የቀረበ፣ የጌታን ልብ ያወቀ ጸሎት” በማለትም ያሞካሸዋል።

የ“ዲያቆን” አሸናፊ መኮንን፣ አዲሱ ድርሳነ ማርያም (ክፍል ፩)

Please read in PDF
መግቢያ

  “ዲያቆን” አሸናፊ መኮንን፣ የዮሐንስ ወንጌልን እያንዳንዱን ምዕራፍ በመተርጐም፣ የዮሐንስ ወንጌልን ምዕራፍ ኹለትን፣ ኹለተኛ መጽሐፍ በማድረግ አቅርቦታል፤ ለምዕራፍ ኹለቱ መጽሐፍ፣ የሰጠው ርእስ “ቃና ዘገሊላ” የሚል ሲኾን፣ መጽሐፉ 252 ገጻት፣ አሥራ አምስት ክፍሎች[ምዕራፍ ሳይኾን] አሉት። መጽሐፉ የተጻፈው የዮሐንስ ወንጌልን ማዕከል በማድረግና “የለዘብተኞችን ንቅናቄ አራማጆችን ትምህርታቸውን እየነቀፈ” መተርጐምና ትችትን ማቅረብ እንደ ኾነ ጠቅሶአል፤ በተጨማሪም መጽሐፉ ራሱ የተወለደው፣ ከዮሐንስ ወንጌል ጥልቅ ምስጢር እንደ ኾነም ጭምር በድፍረት በመናገር።1

Monday, 6 April 2020

ኒቆዲሞስ - የሰው ጽድቅ ሽማግሌ - የኢየሱስ ሕፃን

Please read in PDF
  በዓቢይ ጾም ውስጥ ስያሜ ከተሰጣቸው ሳምንታት፣ ያለንበት ሳምንት ኒቆዲሞስ ተብሎ ይጠራል። ታሪኩ የሚገኘው በዮሐንስ ወንጌል ምዕ. 3፥1-21 ባለው ክፍል ውስጥ ነው። ኒቆዲሞስ በትውልዱ አይሁዳዊ ቢኾንም፣ ስሙ ግን የግሪክ ስም ነው። አይሁዳዊ ኾኖ፣ የግሪክ ስም መያዙ በራሱ ያስደንቃል፤ አሕዛብን አጥብቀው ከሚንቁና ከሚጠሉ ፈሪሳውያን መካከል መገኘቱና አለቃቸው መኾኑ ደግሞ፣ እጅግ አስደማሚ ነው። በክፉዎች መካከል፣ ከክፉዎች መካከል የተገኘ ደገኛና የሰላም ሰው ነበር። ይህ ብዙ ጊዜ ሲኾን አይታይም።

Tuesday, 31 March 2020

ቀጥ ያለ ኦርቶዶክስ!

መብራቴ እንደ በራ ጨዌ እንደ ሰማ
ውስጤ እንደ ፈለገ የክብርህን ግርማ
አጊኝቼ ልራብህ አይቼ ልናፍቅህ

Monday, 30 March 2020

የገነነ ምሕረት!

በምድራችን ላይ እጅግ አያሌ ተላላፊ በሽታዎች ተነስተዋል፤ እስካሁን ግን ከ1918 እስከ 1919 ዓመተ እግዚእ፣ የዓለማችንን 50 ሚሊየን ሕዝብ ቅርጥፍ አድርጎ የበላ፤ እንደ ቅጠልም  ያረገፈ፤ በH1N1 Virus መነሻነት የተነሳውና “Spanish flu” በመባል እንደሚታወቀው መረርሽኝ ያህል የተነሣ የለም፡፡ በጊዜው የዓለማችን አንድ ሦስተኛው የሚያህለው ማለትም፣ 500 ሚሊየን ሕዝብ ገደማ በቫይረሱ ተጠቅቶ ነበር፤ ከዚህ ቁጥር ውስጥ ደግሞ 50 ሚሊየን ገደማ ሕዝብ ሞቶ ነበር፤ የዚያኔ በአሜሪካ ብቻ 675 ሺህ ሕዝብ ያህል አልቆባት ነበር፡፡

Saturday, 28 March 2020

ስለ ኮሮና የእግዚአብሔር ልብ ምን ይላል?!


 
   እግዚአብሔር ይህችን ምድር በእሳት ትኩሳት ሊያሳልፋት ቀጠሮ የያዘላት እንጂ ዘላለማዊና ቋሚ፣ ደስታዋም የማይከስም ኾና የተሠራች አይደለችም፤ ምድርና ሥጋ በእርጅና ይያዛሉ፤ ያረጃሉ፣ ይጃጃሉ፣ ይገረጅፋሉ፣ እንደ ብራናም ተጠቅልለው ያልፋሉ፤ እንደ አበባ ይረግፋሉ፣ እንደ ቅጠል ይጠወልጋሉ፣ እንደ ሣር ደርቀው ይጠፋሉ (1ጴጥ. 124) የእግዚአብሔር ቃል ግን አይሻርም፤ ደግሞም ለዘላለም ጸንቶ ኗሪ ነው፤ (1ጴጥ. 125 ዮሐ. 1035) ከቅዱስ ቃሉ የሚመዘዙት ፍርዱ ደግሞ እውነትና ቅንነት የከበባቸው፣ እጅግም ጣፋጭ ናቸው፤ (መዝ. 199-10)



Friday, 27 March 2020

በቫይረሱ ብንያዝስ?



በኮሮና ቫይረስ ከተያዙ ወይም ተይዣለው ብለው ከጠርጠሩ ምን ማድረግ ይችላሉ ?
ሳል፣ ትኩሳት፣ ትንፋሽ ማጠር እና ተያያዝ ምልክቶች በራስዎ ላይ ከተመለከቱና በኮቪድ-19 እንደተጠቃ ከሚጠረጥሩት ወይም ከተረጋገጠ ሰው ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ከነበርዎት ወይም በኮቪድ19 ወደተጠቁ አገራት/አካባቢዎች ተጉዘው ከነበረ ምን ማድረግ አለብዎት?

Wednesday, 25 March 2020

ለሚበልጠው ብልጥግና ትጉ!

Please read in PDF
   ከቅርብ ጊዜ ወዲህ “ለጤናማ ብልጥግና ትጉ፣ ለጤናማ ብልጥግና መትጋት ይገባናል” የሚሉ አባባሎች፣ በመካከላችን አሰምተው ሲነገሩ እየሰማን ነው። አባባሉ ጤናማ ቢመስልም፣ በውስጡ ግን ስውር መደላድል የለውም ማለት፣ እጅግ ተላላነት ሊኾን ይችላል። “የብልጥግና ወንጌል” መምህራንና ደቀ መዛሙርት ዋና ቅኝታቸው፣ መጽሐፍ ቅዱስን በመታከክ ለብ ያሉ መልእክቶች ማቅረብና ማስተላለፍ እንደ ኾነ መዘንጋት አይገባንምና።  ለብ ያለ ነገር ደግሞ ለፍጥረታዊው ሰው እጅግ ከመለድለዱም ባሻገር፣ ቀላልና ሰፊ ኹሉም ለመጓዝ የሚያመቸው መንገድ ነው።