Tuesday, 19 April 2016

በጋምቤላ ፤ በሜድትራኒያን ዳርቻ … የሆነው፥ ለእኛ የ“ንስሐ ግቡ” ደወል ይሆን?




“አባቶቻችሁም እንደ ነበሩ አንገተ ደንዳና አትሁኑ ፤ እጃችሁንም ለእግዚአብሔር ስጡ፥ ለዘላለም ወደ ተቀደሰው ወደ መቅደሱም ግቡ፥ ጽኑ ቍጣውም ከእናንተ እንዲመለስ አምላካችሁን እግዚአብሔርን አምልኩ። አምላካችሁም እግዚአብሔር ቸርና መሐሪ ነውና፥ ወደ እርሱም ብትመለሱ ፊቱን ከእናንተ አያዞርምና ወደ እግዚአብሔር ብትመለሱ ወንድሞቻችሁና ልጆቻችሁ በማረኩአቸው ፊት ምሕረትን ያገኛሉ፥ ደግሞም ወደዚህች ምድር ይመለሳሉ።” (2ዜና.30፥8-9)


    ከወደጋምቤላ እናት እስካዘለችው ልጇ ድረስ ተቀልታ በጠቅላላ ከ148 ሰዎች መታረዳቸውን ሰምተን ጆሮዋችን ሳያባራ፥ ከወደሜድትራኒያን ባሕር ዳርቻ ደግሞ ትውልደ ኢትዮጲያውንና ኤርትራውያን ይበዙበታል በተባለ የስደተኞች የባሕር ጉዞ ጀልባ ተገልብጦ ከ400 በላይ ሰዎች መሞታቸውን ተረዳን፡፡ የዛሬ ዓመት ገደማ ኢትዮጲያውያን በዚሁ በሜድትራኒያን ባሕር ዳርቻ በሰው በላው አይ ኤስ አይ ኤስ ዜጎቻችን እንደዋዛ እንደበግ ታርደው ደማቸው በከንቱ ከባሕር ጋር ተቀላቀለ፡፡

Sunday, 17 April 2016

ኒቆዲሞስ - ከውኃውና ከመንፈሱ የመወለድ ምስጢር (ዮሐ.3፥5)


“እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም።” (ዮሐ.3፥5)

   ኒቆዲሞስ የማታ ተማሪ ቢሆንም መምሕር ተብሎም ተጠርቷል ፤ ምናልባት ቀን ቀን ሕዝብ በተሰበሰበበትና ጌታን ዙርያውን ሕዝብ በከበበበት ሁኔታ እንደልብ ለመወያየት ስለማይመች ወይም በማታው ክፍለ ጊዜ በደንብ እንወደደው ሊያወራውና ከእርሱ ሊማር ወይም የአይሁድ አለቃ ስለሆነ በቀን መምጣትን ስለፈራ ሊሆን ይችላል፥ ሌሊቱን በቋሚ ተማሪነት በመምጣት የተጋው፡፡ ባለ ሥልጣን እንደመሆኑ መጠን ሰው ሳይልክ ራሱ መምጣቱ ሊማር ፤ ሊረዳ ከልቡ መውደዱን ፤ የመንፈስ ጥማትም ያለበት መሆኑን እናስተውላለን፡፡ ከጌታ ለመማር እርሱ ድካምና ዝለት ፤ ሌሊትና ቀን የማይፈራረቅበት የዘላለም መምህር ነው፡፡ ሲያስተምር በቅንነት ነው፡፡ ከታወቁ ሊቃውንትና ፕሮፌሰሮች የሚማሩ እጅግ ይደነቃሉ ፤ ከእርሱ የሚማሩ ግን እጅግ የተወደዱ ናቸው፡፡

Friday, 15 April 2016

አገርም፥ ይህን ያህል ይዘነጋል ለካ!




  መርሳት የተፈጥሮ ባህርያችን ነው ፤ ነገር ግን ጤነኞችና ኃላፊነት የሚሰማን ከሆነ ለዘወትር ልንዘነጋቸው የማይገቡን ነገሮች አሉ፡፡ በጦር ሜዳ ያለ ወታደር ትጥቅና የጦር መሣርያውን ፣ በሙሽርነት ያለች ሴት መጌጥና መዋብን ፣ በበሽተኞች የተከበበ ዶክተርና የሕክምና ባለሙያ ስለሚያክምባቸው የሕክምና መሣርያዎች ፍጹም ሊዘነጉ ከማይችሉ ጥቂት ነገሮች መካከል ናቸው፡፡ እነዚህንና ተመሳሳይ ነገሮችን መርሳት በሕይወት ጭምር አላስፈላጊ ዋጋ ያስከፍላሉ፡፡
   ከምንም በላይ ደግሞ ሕዝብን ለማገልገል በኃላፊነት የተቀመጥን ሰዎች ዘወትር ልመናችን እንደንጉሥ ሰሎሞን ብዙ ሃብትና ብዕል እንዲሰጠን ከመመኘት ይልቅ ሕዝቡን መምራት የሚያስችለንን ማስተዋልና ጥበብን እንዲሰጠን ቢሆን መልካም ነው፡፡ ሰሎሞን ይህንን ስለለመነ (1ነገ.3፥11)፥ “እግዚአብሔርም ለሰሎሞን እጅግ ብዙ ጥበብና ማስተዋል በባሕርም ዳር እንዳለ አሸዋ የልብ ስፋት ሰጠው።” (1ነገ.4፥29) ብሎ ቃሉ ይነግረናል፡፡ ልበ ሰፊነት ብዙ የሚመረምርና የሚያሰላስል ልብ ስለሆነ በዝንጋኤ የማይጠቃ አስተዋይ ልብ ነው፡፡

Sunday, 10 April 2016

ገብር ኄር - ለክርስቶስ ባሮች እንጂ ሎሌዎች አይደለንም!

    
  “ገና ያልተሰናሰናለው” ዘመናዊው መናፍቅነት የሆነው፥ ድኅረ ዘመናዊነት ወጣቱን ትውልድና “አዳዲሶቹን አማኞች” እያነሆለለበትና ኃጢአትን ያለገደብ ለማለማመድና ለማስፈጸም ከሚጠቀምበት አንዱ ማቀንቀኛ ሃሳቡ፥ “ሰው ነጻ ፍጡር ፤ ለማንም የመገዛት ግዴታ የለበትም ፤ ተገዝቶም አያውቅም” የሚል የጸና አቋም አለው፡፡ ይህ አባባል ሁለት ነገሮችን ሊናገሩበት ያሰቡ ያስመስላቸዋል ፤ (1) ድኅረ ዘመናዊነትን በልካቸው ለብሰው የታዩት አብዛኛዎቹ ምዕራባውያን ከፈሪሃ እግዚአብሔር ተፋተው “በፊታቸው መልካም መስሎ የታያቸውን በማድረግ፥ ለምናደርገው ነገር ሁሉ ኃላፊነቱን የፈጠረን ይውሰድ የሚል ኅሊና ቢስ ምክንያት ሲያቀርቡ ፤ (2) እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ሲፈጥረው የሰጠውን የምርጫ ነጻነት አጣመው ይተረጉሙታል፡፡

Wednesday, 6 April 2016

... የዋጠውን እንመነው!



አልማዝ ወርቅ እንቁውን፣ በኲራቱ ያደበሰ፤
ዘረ አዳምን አስጎንብሶ ፣ ብርታት አቅሉን ያፈረሰ፤

Sunday, 3 April 2016

ደብረ ዘይት - ጌታ ይመጣል!



     መናፍቃን ከሚክዷቸው የክርስትና መሠረተ ትምህርት አንዱ የክርስቶስን በክበበ ትስብእት ፤ በግርማ መለኮት ዳግመኛ መምጣት ነው፡፡ የክርስቶስ ዳግም መምጣት ትምህርት ክርስትናና አስተምኅሮው የተመሠረተበትና የቆመበት ዋና ዓለቱ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ የዳግመኛ መምጣትን ትምህርት ስናነሳ በአብሮነት የሙታንን ትንሣኤ ትምህርት በአንድነት ማንሳታችን የግድ ነው፡፡ ሁለቱ ትምህርቶች ሰፋፊና በየራሳቸው መቆም የሚቻላቸው ቢሆኑም፥ ተያያዥና የማይነጣጠሉ ዋና ዓምዶች ናቸው፡፡
       ቅዱስ ሐዋርያ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፦
“በጌታ ቃል የምንላችሁ ይህ ነውና፤ እኛ ሕያዋን ሆነን ጌታ እስኪመጣ ድረስ የምንቀር ያንቀላፉቱን አንቀድምም፤ ጌታ ራሱ በትእዛዝ በመላእክትም አለቃ ድምፅ በእግዚአብሔርም መለከት ከሰማይ ይወርዳልና፥ በክርስቶስም የሞቱ አስቀድመው ይነሣሉ፤ከዚያም በኋላ እኛ ሕያዋን ሆነን የምንቀረው፥ ጌታን በአየር ለመቀበል ከእነርሱ ጋር በደመና እንነጠቃለን፤ እንዲሁም ሁልጊዜ ከጌታ ጋር እንሆናለን። ስለዚህ እርስ በርሳችሁ በዚህ ቃል ተጽናኑ።” (1ተሰ.4፥15-18) (ለአጽንዖት የተሠመረበት የእኔ ብቻ ነው)

Sunday, 27 March 2016

መፃጉዕ - ለአገሬ፥ ሰው የሚሆንላት ማን ይሆን!?

    
 ዜመኛው ቅዱስ ያሬድ የዓቢይን ጾም ሳምንታት በሰየመበት ስያሜው፥ ይህን ሳምንት መፃጉዕ ብሎ ሰይሞታል፡፡ ትርጓሜው በቁሙ ሲፈታ “ጐባጣ” ማለት እንደሆነ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ(አለቃ) መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ በሚለው መዝገበ ቃላቸው ገጽ 605 ላይ ፈትተውታል፡፡ ለስያሜው መሰጠት ምክንያቱ ደግሞ ቅዱስ ያሬድ የአጽዋማቱን ሳምንታት ስያሜዎች ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲወርሰው አድርጎታል፡፡ ይህ ስያሜም በምን ምክንያት ከጌታ ጋር እንደተገናኘ ሲናገር እንዲህ አለ፦
“በሰንበት ቀን ኢየሱስ ታላላቅ ተአምራትን ያደርግ ነበር፡፡ ከዚህ ሁሉ የሚበልጥ ያደረገውንም እናገራለሁ፡፡ ጭቃ ደህናውን ዓይን ያጠፋል፣ እርሱ ግን በምድር ላይ ተፍቶ ጭቃ አድርጎ ዕውር ሆኖ የተወለደውን አዳነ፡፡ ይህ ግሩም ምስጢር ነው፡፡”

Friday, 25 March 2016

ቀሲስ የ“ክብረት ልጅ”፥ ምነው በስድብ ቃል በጣም ጮኸ?!

 የክብረት ልጅ እይታዎቹን በሚያቀርብበት ብሎጉ፥ “ፓትርያርኩ፦ ለኢትዮጲያ የደኅንነት ፣ ለምእመናን የድኅነት ሥጋት” በሚል አንድ ጽሁፍ፥ ዛሬ አስነብቦ ድንገት ያየ ሰው ጠቆመኝና ወደጡመራው መድረኩ ገብቼ አነበብኩት፡፡ ዳንኤል በዚህ ጽሁፉ “100% ማኅበረ ቅዱሳን ሊያዘጋጀው ከጫፍ የደረሰውን ዐውደ ርእይ የከለከሉት ፤ ያስከለከሉት ፓትርያርኩ ናቸው”፥ ብሎ ደምድሞ አስቀምጦታል፡፡ የዐውደ ርእዩ ባለቤት ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ፥ በዋናው ጸሐፊው አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ በኩል ትላንት ማምሻውን ለጋዜጠኞች በሰጠው ጋዜጣዊ “መግለጫ”፥ “ለመታገዱ ፓትርያርኩ እንደሌሉበትና በመንግሥት አካላት መመሪያ መታገዱን”ይፋዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ 

Wednesday, 23 March 2016

“ከአሜን ባሻገር”፥ ባንሻገርስ!?




ከእግዜር እያፋቱ
ለዝሙት አዲስ በር እየከፋፈቱ
ዘረኝነት “ጠልቶ”
በሰው ልብ አዲስ ዘር ለማብቀል ኮትኩቶ

Monday, 21 March 2016

እስኪ አምጡ ዝምታ!!!


የሰባ መሥዋዕት
ለቁጥር ‘ሚታክት
ያማረ እህል ቁርባን
በኵሩ መልከ መልካም ...

Saturday, 19 March 2016

ባለፉት ሦስት አመታት ...

   

     ባለፉት ሦስት ዓመታት ከሁለት መቶ በላይ የሚሆኑ ከእግዚአብሔር ቃል አንጻር ወቅታዊ ጽሁፎችን ስብከቶችን ትምህርቶችን ግጥሞችን ...ከተወሰኑት ጊዜያት መቋረጥ በቀር በተከታታይ ለማቅረብ ጥሬያለሁ፡፡ በእነዚህ ሦስት ዓመታት ውስጥ ለእግዚአብሔርና ለቃሉ እንጂ ወደማንም እንዳላደላሁ ሕሊናዬ ይመሰክርልኛል፡፡ ከእግዚአብሔር በቀር ማንንም ደስ ለማሰኘትም ሆነ በከንቱ ለመውቀስ እንዳልተጋሁም እንዲሁ፡፡

Tuesday, 15 March 2016

ወርሰን ያንተን ደስታ

                                           
                                                 Please raed in PDF

ያኔ …
ሥላሴ በስድስተኛው ቀን
ፈጥሮ ፤ ፈጽሞ አረፈ እረፍትን ፤

Thursday, 10 March 2016

ክርስቲያን ያልሆኑት ኦርቶክሳውያን ወይስ ምህረተ አብ?! (የመጨረሻ ክፍል)

የኦርቶዶክስ የት መጣ
    “ኦርቶዶክስ” የሚለው ስም ስያሜ ዋና መሠረቱ ትምህርተ ክርስትና [1] ነው፡፡ ቅድመ ኒቂያና ድኅረ ኒቂያ (pre Nicene) ማለትም፥ ከ300-325 ዓ.ም ገደማ እና ድኅረ ኒቂያ (post Nicene) ከሌሎቹ መናፍቃን ይልቅ አርዮስ ወልድና መንፈስ ቅዱስ ላይ ጠንካራ የክህደት ትምህርቱን አሰማ፡፡ በ325 ዓ.ም ሦስት መቶ አሥራ ስምንቱ የቤተ ክርስቲያን አባቶች አርዮስን [2] በክህደቱ ባወገዙበት ወቅት አርዮስን ያወገዙበትን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርታቸውን “ኦርቶዶክስ” ብለው ሰየሙት፡፡

Saturday, 5 March 2016

ጌታ ኢየሱስ ከሰማያት የወረደው አምላክነትን ሊሾም አይደለም!

   Please read in PDF

  የዓቢይ ጾም ፊተኛው ሳምንት መጠርያ ዘወረደ ይባላል፡፡ ይህም ክርስቶስ ኢየሱስ ከሰማየ ሰማያት የሰው ልጆችን ለማዳን በእርሱ ፤ በአባቱና በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ መምጣቱን ቤተ ክርስቲያን በአምልኮዋ ትዘክረዋለች፡፡ እርሱ የወረደው እኛን ለማዳን ነው፡፡ ምክንያቱም ከሰው ወገን ወይም ከፍጡር ወገን ማንም እኛን ማዳን ስላልተቻለው አካላዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ በገዛ ፈቃዱ ሊያድነን መጣ፡፡  ዛሬ ይህ እኛን ለማዳን ከሰማያት የወረደው ጌታ፥ ስለመውረዱእየተነገሩ ያሉ ብዙ ክህደቶች አሉ፡፡
     ከግኖስቲካውያን እስከ ዶሴቲክስ ፤ ከአርዮስ እስከ ንስጥሮስ ፤ ከሞርሞናውያን እስከ ኦንሊ ጂሰሶች ፤ ከይሖዋ የመንግሥት አዳራሽ ምስክሮች እስከ ዘመነኞቹ የአዲሱ ትውልድ እንቅስቃሴ (New age Movement) ፤ የእምነት እንቅስቃሴ (Faith Movement) እና Biblical Unitarian እስከሚባሉት ድረስ ለዘመናት መናፍቃን መልካቸውን እየቀያየሩ በጌታ ኢየሱስ ላይ እጅግ አጸያፊ ክህደቶችን አውርደዋል ፤ አሁንም አላባሩም፡፡ ከሚያደርሱትና እያደረሱ ካሉት ጥፋት አንጻር ግን ቤተ ክርስቲያን ሥራዋን በአግባቡ እየተወጣች ነው ለማት አያስደፍርም፡፡

Sunday, 28 February 2016

ወንድሜ ማን ነው? (የመጨረሻው ክፍል)

ከማይጠፋ ዘር ተወልደን ወንድማማች የሆንበት ምስጢር
     ጌታ ኢየሱስ ከባሕርይ አባቱ ከአብ የተወለደ ፍጹም ልጅ ነው፡፡ በእርሱ ልጅነት እኛ ደግሞ ልጆች ተብለናል፡፡ በዓመጽና ባለመታዘዝ ፊተኛው አዳም የእግዚአብሔር ልጅነትን ሲያጣ ሁለተኛው አዳም እግዚአብሔር ወልድ እንደልጅ ፍጹም በመታዘዝ (ዕብ.5፥8) ሁላችን ለእግዚአብሔር ልጆች እንሆን ዘንድ እርሱ በኵር ሆነ፡፡ እኛ ወደአባቱና ወደእርሱ ክብር የምንገባው የእርሱን “አማኑኤልነት” አብነት አድርገን ነው፡፡ የቀደመው አዳም ከኃጢአት የተነሳ ለሞት ወልዶን ነበርና፡፡
    ከማይጠፋ ዘር ስለመወለድ ወይም ስለዳግም ልደት ስንናገር በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መፈጠርን ወይም ፍጹም መለወጥን የሚያሳይ ነው፡፡ መፈጠር የሚለው ቃል አዲስ ማንነትን ማግኘትን ያሳያል ፤ ከዚህም የተነሣ ከእግዚአብሔር የሆነ የዘላለም ሕይወት ሠርጾ በአማኙ ልብ ውስጥ ይገባል፡፡ (ዮሐ.3፥16 ፤ 2ጴጥ.1፥4 ፤ 1ዮሐ.5፥11) አማኙም በእምነት ጌታ ኢየሱስን ተቀብሎታልና ፍጹም የእግዚአብሔር ልጅ ይሆናል (ዮሐ.1፥12 ፤ ሮሜ.8፥16 ፤ ገላ.3፥26) ፤ አዲስ ሰውነትን (2ቆሮ.5፥17 ፤ ቈላ.3፥9) የዘላለም ሕይወት (1ዮሐ.5፥20) ያገኛል፡፡