Wednesday, 30 April 2014

መስቀል ላይ ያላችሁ!

Read in PDF: Meskel Lay yalacheu

 ሥቁል ነኝ ለዓለም የማልረባ ባዶ
እርሷም በእኔ ፊት ፍሬ የሌላት ነዶ
የዓለምን አምሮት ቋቅ እንትፍ አድርጌ
በሞት ኢየሱስን ደግሞም በመቃብሬ
አንድ ሆኛለሁ ሎሌው በእርሱ በዝቶ ክብሬ፡፡

Sunday, 27 April 2014

ደቀ መዛሙርት የጌታን ትንሳኤ ለምን ተጠራጠሩ?(ክፍል - 1)

    “ትንሳኤ ሙታንስ ከሌለ ክርስቶስ አልተነሳማ፤ክርስቶስም ካልተነሳ እንግዲያስ ስብከታችን ከንቱ ነው እምነታችሁም ከንቱ ናት፤ደግሞም ክርስቶስን አስነስቶታል ብለን በእግዚአብሔር ላይ ስለመሰከርን ሐሰተኞች የእግዚአብሔር ምስክሮች ሆነን ተገኝተናል … ፡፡”(1ቆሮ.15፥13-16)
   “የክርስቲያን የሃይማኖት ትምህርት መነሻና መድረሻ፣በሞትና በትንሳኤ ጉዳይ ላይ ያተኮረ ነው ቢባል ከእውነት የራቀ አይሆንም፡፡” (አበራ በቀለ(ሊቀ ጉባኤ አባ)፡፡(1996)፡፡ትምህርተ ሃይማኖት እና ክርስቲያናዊ ህይወት፡፡አዲስ አበባ፡፡ንግድ ማተሚያ ድርጅት(ማህበረ ቅዱሳን)፡፡ገጽ.209)

   “የክርስቶስ ትንሳኤ ለክርስቶስ አምላክና ለክርስቲያናዊ ትምህርታችን እውነተኛነት ከፍተኛ ምስክር ነው፤ምክንያቱም ክርስቶስ ሲገረፍ፤ሲዋረድ፤ሲሰቀል እንደዕሩቅ ብእሲ ተቆጥሮ ነበር፤ደካማም መስሎ ተገምቶ ነበርና፤ በመለኮታዊ ሥልጣኑ ሞትን አሸንፎ ሲነሳ ግን አምላክነቱን ኃያልነቱን ገልጧልና፡፡ እንዲሁም ክርስቶስ የተናገረው ያስተማረው ሁሉ ማጠቃለያው ትንሳኤው ስለሆነ ነው፡፡” (መልከጼዴቅ(አባ)፡፡1984፡፡ትምህርተ ክርስትና ፪ኛ፡፡አዲስ አበባ፡፡ትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ድርጅት፡፡ገጽ.59

     ከመሠረታውያን የክርስትና ትምህርት አንዱና ዋናው የጌታን ትንሳኤ ማመንና መቀበል ነው፡፡የጌታን ትንሳኤ አለማመን ወይም መጠራጠር በጠቅላላ ክርስትናን እንደመካድ ይቆጠራል፤ከመናፍቃን እንደአንዱም ያስደምራል፡፡“ክርስቶስ ካልተነሳ እምነታችን ከንቱ ናት እስከአሁን ድረስ በኃጢአት አለን” ማለትን ያስደፍራል፡፡(1ቆሮ.15፥17) የክርስትና እምነት መገለጥ ነው፤እግዚአብሔር ራሱን በልጁ ገለጠልን፤ራሱ እግዚአብሔርም ከእኛ እንደአንዱ ሆኖ በእኛ መካከል ለእኛ ተገለጠ፡፡የዚህ ትምህርትና እምነት መደምደሚያ የተስፋውን ነገር ስናምን ነው፡፡ትልቁ የተስፋ ትምህርት ደግሞ የክርስቶስን ትንሳኤ በማመን የሙታንን ትንሳኤ ተስፋ ማድረግ ነው፡፡“የሙታንንም መነሳት ተስፋ እናደርጋለንና”፡፡(አንቀጸ ሃይማኖት)

Tuesday, 22 April 2014

"ዘፋኝ" ለኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ምኗ ነው?

Please read in PDF :- zefagn lebetekiristiyan mnua new?
ከሰሞኑ አንድ ዘፋኝ “ከወንጌላውያን ህብረት አብያተ ክርስቲያናት አባል ነህ” ያሉትን ድህረ ገፆችና  መገናኛ ብዙሀን እንደሚከሰና እርሱ “ኦርቶዶክሳዊ” እንደሆነ ማረጋገጫ እንዲሰጡት፤ይቅርታ  እንዲጠይቁትም ሊያደርግ  እንዳሰበ ከመገናኛ  ብዙሀን  ሰምተናል፡፡“ተደንቀናልም”፡፡ ለመሆኑ “ዘፋኝ” ለኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን  ምኗ  ነው? አማት ወይስ ምራት? አጎት ወይስ  አክስት? “የወንጌላውያን ህብረት አብያተ ክርስቲያናት” ዓለም  ያከበረቻቸው  ሰዎች ሲመለሱላቸው “የሚደሰቱት”፤ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ዓለም ያከበረቻቸውን እርሷም አብራ በመመቻመች የሚዘልቁት እስከመቼ  ነው? (ምነው የትም በጭፈራ እያሳለፉ የዚህ እምነት ተከታይ ነበርኩ ዛሬ ጌታ “ተገለጠልኝ” ማለት አልበዛም እንዴ?)

    አንደራደርም ፤“ዘፋኝነት” (አዲሱ “የቤተ-ክርስቲያናችን  መጽሐፍ  ቅዱስ” ባይጠቅሰውም) የሥጋ ሥራ ነው፡፡(ገላ.5፥21) የሥጋን ሥራ የሚያደርግ ሁሉ ደግሞ የእግዚአብሔርን  መንግስት  አይወርስም፡፡ (1ቆሮ. 6፥11) በክርስቶስና በእግዚአብሔር መንግስትም ርስት የለውም፡፡(ኤፌ.5፥5)፡፡እርግጥ ነው በቀደመው ዘመን ሁላችን የኃጢአት ባርያዎች፤ የሞትም አገልጋዮች ነበርን፡፡ ነገር ግን ዛሬ ከዚያ ከምናፍርበትና ከምንፀፀትበት ህይወታችን ያተረፍነው ምንም ፍሬ ስለሌለን፤ መጨረሻውም ሞት እንደሆነም ስላመንን፤ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆነን አሁን ከኩነኔ ነፃ ነን፡፡(ሮሜ 6፥20፤8፥1) ባዕለጠጋው እግዚአብሔር  ‹‹ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩም የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ህይወትን ሰጠን፤ በፀጋውም አዳነን››፡፡(ኤፌ.2፥4-6)

Saturday, 19 April 2014

“ከጾመም በኋላ ተራበ፡፡”(ማቴ.4፥2)


Please read in PDF:- ከጾመም በኋላ ተራበ

      ጾማችንን የልማድና መለኮታዊ ኃይል አልባ ከሚያደርጉት ነገሮች አንዱ ከጾምን በኋላ የመብላትና የመጠጣት ፍላጎት እንጂ መንፈሳዊነትን በመራብ መሻትና ፍለጋ በውስጣችን አለመኖሩ ነው፡፡ጌታ ኢየሱስ የይፋ አገልግሎት ከመጀመሩ በፊት አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾሟል፡፡ጌታ እንደጾመም ተፈትኗል፡፡የተፈተነው በዲያብሎስ ነው፡፡የፈተናው መጀመርያ ደግሞ በመብልና በመጠጥ ነበር፡፡እኛ ለመብላትና ለመጥገብ ስንጾም ጌታ ኢየሱስ ግን ለመራብና “ለትልቅ መለኮታዊ ዓላማ” ጾመ፡፡
 ጌታ ኢየሱስ እንደዘመኑ አባባል ኃጢአት ስለነበረበት የኃጢአት ሥርየት ሊያገኝ አልጾመም፡፡ ጌታ ኢየሱስ ኃጢአት የማድረግ ፍላጎትም ሆነ ዝንባሌ የሌለው፣በተግባሩ፣በንግግሩና በመንፈሱ ፈጽሞ ኃጢአት ያልፈጸመ ነው፡፡እርሱ ኃጢአትን አያውቅም፤አላደረገምም፤ተንኮልም በአፉ ያልተገኘበት … (2ቆሮ.5፥21 ፤1ጴጥ.2፥22) ቅዱስና ያለተንኰል ነውርም የሌለበት ከኃጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለና(ዕብ.7፥26) በእርሱም ኃጢአት የሌለ ነው፡፡ (1ዮሐ.3፥5) ስለኃጢአት ማንም እርሱን መውቀስ አይቻለውም፡፡(ዮሐ.8፥46)፡፡ ይህ ንጹህና ጻድቅ ጌታ ግን ከጾመ በኋላ ተራበ፡፡መራቡ ደግሞ ግልጥ ፈተና ይዞ መጣ፡፡
  የጌታ ኢየሱስ በዲያብሎስ መፈተን ለአርዓያ የሆነ ወይም የቀረበ አይደለም፤በእውነትም እርሱ ተፈትኗል፡፡“ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደእኛ የተፈተነ …”(ዕብ.4፥17)፣ “ተፈትኖም መከራን የተቀበለ” (ዕብ.2፥15) ነው፡፡ ዲያብሎስ በምሳሌነት ሳይሆን በእውነትም ፈትኖታል፡፡ጌታ ኢየሱስ ከሰማያት ወደእኛ የመጣው በጸጋው ቃል ለድሆች ወንጌልን ሊሰብክ፣የታሰሩትን ሊፈታና በተአምራቱ የተጠቁትን ነጻ በማውጣት የተወደደችውን የጌታ ዓመት ይሰብክ ዘንድ ነው፡፡(ሉቃ.4፥17) ይህ ደግሞ “መለኮታዊ ዝግጅት” ያስፈልገዋል፡፡ የቃል ኪዳኑን ሰነድ ሙሴ ሊቀበል አርባ ቀንና አርባ ሌሊት፣ኤልያስም እስከእግዚአብሔር ተራራ ድረስ ለመጓዝ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾምን ጾመዋል፡፡ጌታ ኢየሱስም የአባቱን ፈቃድ ሊፈጽም ጾመ፡፡
  ከጾማችን በኋላ ትልቅ ሥራ፤ ትልቅ የመንፈስ ቅዱስ መቀባት ከሌለ ጾሙ ልማድ ወይም ከረሃብ አድማ ያለፈ ሌላ ትርጉም የለውም፡፡ ሙሴም ኤልያስም ከጾማቸው በኋላ ታላላቅ ሥራዎችን ሠርተዋል፡፡(ዘፀ.34፥28፤1ነገ.19፥8) ከእግዚአብሔር ቅዱሳን የምናየው ትልቁ እውነት ከዝግጅት በኋላ ትልቅ ድል በሠራዊት ጌታ ጉልበት እንደሚቀዳጁ ነው፡፡መርዶክዮስ፣ አስቴርና በሱሳ ግንብ ሥር የነበሩት አይሁድ ከጾሙ በኋላ ታሪክ ገለበጡ፡፡(አስ.8፥4) የነነዌ ሰዎች ከጾሙ በኋላ ቁጣ በረደላቸው(ዮና.3፥10) … ብዙ ቅዱሳንና የእግዚአብሔር ህዝቦች ከጾምና በፊቱ ከመማለድ በኋላ የተወደደ መልስን ከጌታ ዘንድ አጊኝተዋል፡፡እኛ በጾም ተርበን ሳንፈተን  በራሳችን እጅ በዶሮና በበሬ ሥጋ፤በዝሙትና በሙዚቃ ኮንሰርት የኃጢአቱን ፈተና በሰይጣናዊ ንስሐ እንመልሳለን፡፡

Friday, 18 April 2014

መካከለኛው መስቀል

ለሁለት ሺህ ዘመናት ግለቱ ያልቀዘቀዘ፣ ኃጥአንን የማረከ፣ መናንያንን ከፍጡር ፍቅር ለይቶ ያመነነ፣ ደናግላንን “የዘመኔ ጌታ አንተ ነህ” እንዲሉ ያስመካ፣ ሊቃውንትና መተርጉማን ቀለምና ብራናቸውን አስቀምጠው እንዲመሠጡና እንዲደመሙ ያደረገ፣ ዘማርያን ክብራቸውን ያስጣለና በደስታ ያዘለለ፣ህጻናት ማር አንደበታቸው እየጣፈጠ የተናገሩለት፣ ሰማዕታት “ሞት ሆይ፥ መውጊያህ የት አለ? ሲኦል ሆይ፥ ድል መንሣትህ የት አለ?” እያሉ የፎከሩት፣ ሰማይና ምድር የተራረቁት፣ የመለኮትን ክብር እንዳናይ የጋረደን መጋረጃ ከሁለት የተቀደደው ፣ከበረቱና ከመንጋው የተለዩት አህዛብ ወደአንዱ እረኛና ወደመንጋው የተጨመሩት ፣የሚያስጨንቀን ተጠርቆ በሞቱ ከመንገድ የተወገደው፣ አበው “እንዲህ ያለ ሰውን መውደድ አንዴት ያለ ፍቅር ነው?!” ብለው በመገረም የጠየቁት፣በወንበዴነት የዘላለም ባልንጀሮች የነበሩት በህይወቱ ጌታ ምርጫቸው የተለያየበት፣ከምድር እስከሰማይ የሚያድርሰው መካከለኛው መስቀል ጻድቃን የጸደቁበት፣ሰማዕታት የጨከኑበት ፣እናቶች ያነቡለት፣የሚወዱት ያለቀሱለት ድንቅ ምስጢር ነው፡፡
      የመካከለኛው መስቀል ለሁሉም ፍጥረተ አለም የሚማልድና ለሁሉም አዳማዊ ፍጥረትም እኩል እጁንም የዘረጋ ነው፡፡የመስቀሉ ደም ምርጫቸውን በንስሐ ለሚያስተካክሉ ኃጥአን ህይወትና የዘላለም ገነት ነው፡፡የመስቀሉ ደም ከአቤል ደም ይልቅ ምህረትንና የሚሻለውን የሚናገር “የማስተሥረያ ሥርዓት” ሆኖ በአብ ፊት ለኃጢአን ሁሉ የሚቆምና ስለመዳን፣ስለይቅርታ ሳይታክት የሚጮህ ነው፡፡(ዕብ.12፥23)

Wednesday, 16 April 2014

ጌታ ለምን የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ?

መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርገዋል የሚባሉ  ልማዶች በየጊዜው ባለመሰልቸት ሊመረመሩና ሊጤኑ፤ ግድፈት ሲገኝባቸው ሊስተካከሉ፤  መጽሐፍ ቅዱሳዊውን እውነት እንደጨበጡ ያሉ ከሆኑ ደግሞ በፀሎትና በቃሉ ቅጥርነት ሊጠበቁ ይገባቸዋል፡፡ በቤተ-ክርስቲያን ቀኖና  መሠረት ከበዓለ ሥቅለት በፊት ባለው ሐሙስ እግር  የማጠብ ልማድ ስላለ ከታላላቆች ሊቃነ - ጳጳሳት “እንደማዕረጋቸው” እስከታች ያሉቱ የሌሎች “ታናናሾቻቸውን” እግር ያጥባሉ፡፡በዕለቱም ስለትህትና ተገልጦ ይሰበካል፡፡ በእርግጥ እውነተኛ  ትህትና ትልቁ ትንሹን ሲያገለግል እንጂ ትንሹ  ትልቁን ሲያገለግል ብቻ አይደለም፡፡
 በእኛ ማህበረሰብ ውስጥ  “ትልቅ” የተባሉት አካላት ትልቅነታቸውን እንዳስከበሩ መኖር እንጂ ፈፅሞ  ዝቅ ብለው ማገልግል አይሆንላቸውም ቢያደርጉትም በዓመት አንዴ እንደበዓል እንጂ የዕለት ተዕለት በጎ ምግባር ሲሆን አይስተዋልም፡፡ ጌታ ግን ይህ የእግር ማጠብ ሥርዓትም እንደበዓል  በዓመት አንዴ ሳይሆን በየእለቱ እንድናደርገው በፍቅር አዝዞን ነበር፡፡(ዮሐ- 13፥15) ይሁን እንጂ ዘመናችንን ሙሉ ባልጀራችንን እየተጠራጠርን፤ በኑሮዐችን ሁሉ በክፉ ቅንዐት ነቅዘን ያለቅነው፤ ከእኔ ይልቅ የባልንጀራዬ ጥቅም  ይቅደም(ፊሊ.2፥4) ከማለት የተስገበገብነው... የልማድ እግር ማጠብ እንጂ እውነተኛ ትህትና በውስጣችን ስለሌለ ነው፡፡ በተለይ የቤተ-ክርስቲያን መሪዎች፣ የሀገር መሪዎችና  ባዕለሥልጣናት የሾማቸው እግዚአብሔርና አደራ አሳልፎ የሰጣቸውን ህዝብ ሲገዳደሩና ሲዘባነኑበት እንጂ ዝቅ ብለው በትሁት ልብ ሲያገለግሉት ማግኘት እንደ ዔሊ ዘመን የእግዚአብሔር ራዕይና ቃል ብርቅ ነው፡፡ (1ሳሙ.3፥1)

Monday, 14 April 2014

ሆሼዕና ኢየሱስ


Please read in PDF ; hoshena Eyesus
ምድር ነዳ ከስላ  - ጠቋቁራ ጠልሽታ፤
ዙርያዋን በኃጢአት - ነበልባል ተከባ፤
ትዳር መቅኖ አ’ቶ፤
ሴሰኝነት ክንፉን አርብቦ ዘርግቶ፤
ትውልድ በአመጻ መንፈስ ነፍሱ ጎብጦ፤
              እያየኸው አይሙት የሞትክለት ትውልድ
              ሆሼዕና ኢየሱስ ልቡን መልስለት፡፡
ቃየላዊ ብልጠት - ባ’ቤል ደም መጨቅየት፤
በለዓማዊ ብልሐት - የመረረ ርኩሰት፤
የከንፈር አምልኮ - የሽንገላ ፍቅር፤
ድኃውን ከፍትህ - በገንዘብ መፈንገል፤

Monday, 7 April 2014

ኒቆዲሞስ - የአይሁድ አለቃ



በቤተክርስቲያን ቀኖና መሰረት ሰባተኛዉ ሳምንት የጌታ ፆም ስያሜ ኒቆዲሞስ ይባላል፡፡የሚነበበም የቅዱሱ ወንጌል ክፍል ደግሞ ዮሐ.3÷1 ጀምሮ ያለዉ ነዉ፡፡የዮሐንስ ወንጌል እንደሌሎቹ ወንጌላውያን የኢየሱስ ታሪክ ላይ አያተኩርም፡፡ የኢየሱስን ክርስቶስ መሆን እያስረገጠ የአዲስ ኪዳንን የአምልኮ መገለጫና መንፈሳዊነትን እያጎላ የተጻፈ ቅዱስ ወንጌል ነው፡፡ገና ወንጌሉን ሲጀምር አከላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስን ጨለማ የማያሸንፈው፣ ሁሉ በእርሱ የሆነ፣ ጸጋንና እውነትን የተመላ፣ የእኛንም ሥጋ የነሳ ህይወትና ጸጋን አስገኚም ቃል እንደሆነ አበክሮ ይመሰክራል፡፡(ዮሐ.1፥1-15) ጌታ መንፈሳዊ የማያረጅ ልጅነትን ለሽማግሌውና ለትልቁ ባለሥልጣን ለኒቆዲሞስ እንዳስተማረውም የዘገበልን የዮሐንስ ወንጌል ብቻ ነው፡፡
    ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ የሆነ ፈሪሳዊ ባለሥልጣን ነው፡፡በጌታ ኢየሱስ ዘመን ብዙ አይሁድና ፈሪሳውያን ጌታን ያሳድዱት ፤ሊገድሉትም ይፈልጉት ነበር፡፡(ዮሐ.5፥16፤7፥19) የህጉን ምንጭ ክርስቶስን እየተቃወሙ ስለህጉ እንቀናለን ብለው ኢየሱስን ፈጽመው ጠሉት፡፡እነርሱ ከማይወዱትና የገዛ ወገናቸው ሆኖ ካልተቀበሉት (ዮሐ.1፥11) ከዚህ ሰው ጋር ኒቆዲሞስ ብርቱ ወዳጅነትን መሰረተ፡፡ትንሹ ባለሥልጣን ትልቁ ባለሥልጣን ዘንድ ቀርቦ ያወራው የሥልጣኑን ዘለቄታነትና የማርዘሚያውን መንገድ ሳይሆን መንፈሳዊውን እውነት ነው፡፡

Thursday, 3 April 2014

ሁለተኛው መስቀል

Please read in PDF ;- huletegnaw Meskel

ታላቁ መጽሐፍ ቅዱስ የቱ ወንበዴ በግራ እንደተሰቀለ ሳይነግረን፤ ጌታ ግን በሁለቱ ወንበዴዎች መካከል መሰቀሉን ይነግረናል፡፡እንዳለመታደል ግራና በግራ መሆንን ፈጽሞ እንጠላለን፡፡ጸሎታችንም በቀኝ አውለኝ እንጂ በግራ አውለኝን አያካትትም፡፡መቼም ጌታ ፍየሎች(ኃጥአን) በግራ ይቆማሉ ሲል በሰማያዊ ዓለም ግራና ቀኝ አለ ሊለን አይደለም፡፡
     ግራና ጨለማ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍጥረቶች ናቸው፡፡እኛ ግን ለጠላት “ግዛትህ ነው” ብለን ስለለቀቅንለት ቅዱሱ ፍጥረት የጠላት መገለጫ ሆኖ ተገኘ፡፡ጌታ እግዚአብሔር ጨለማ በፊቱ የተገለጠ ብርሃን ነው፡፡ጨለማን ለሰይጣን ሰጥተን ጠልተነው በሰባኪዎቻችንና በመነኮሳቱ ቀሚስ መውደዳችን ግን እጅግ የሚገርም ነው፡፡
      ሰው በቦታ አይከብርም ወይም አያርፍም፡፡እግዚአብሔር ካልቆመበት ቀኝ እግዚአብሔር የቆመበት ግራ ይሻላል፡፡አዳም በውቧ ኤደን ገነት ቢቀመጥም ከእግዚአብሔር ስለተለየ በገነት መካከል ተቀምጦ ስደተኛ ፣ያላረፈ፣ ተቅበዝባዥ … ነበር፡፡ እግዚአብሔር ከሌለባት ገነት እንኳ የስደተኞች ቅዱሳን ማረፊያ አትሆንም፡፡እግዚአብሔር እንጂ ቦታ አያሳርፍም፡፡ዛሬ ብዙ አብያተ ክርስቲያናት በአለም ካለው ኃጢአትና ነውር የማይተናነስ ክፋት ይሰራባቸዋል፡፡ለ“ቅድስና ተለይተው” ከአለሙ ያልተሻሉ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ቦታ ቢያሳርፍ ብዙ አብያተ ክርስቲያናት ለብዙ ኃጢአተኞች ማረፊያ ሆነው በተገኙ ነበር፡፡በአንድ ወቅት በአንድ ቤተ ክርስቲያን ለህንጻ ማሰርያ ገቢ ማሰባሰቢያ ተብሎ በቢራና በሥጋ “የምግብ ባዛር” ተዘጋጅቶ ሳለ ፕሮግራሙን የሚመራው የመድረክ ሰው እንዲህ አለ፦ “ቅዱስ ጊዮርጊስን እየጠጣችሁ በእርሱ ትባረካላችሁ”፡፡(ጠጪዎችና ሰካራሞችን “የሚያጽናና ስብከት”)
     ጥቂት ያይደሉ ገዳማት፣አድባራትና አብያተ ክርስቲያናት በምንም መልኩ ከአለሙ ሥፍራ የማይሻሉ ናቸው፡፡የአምልኮ መልክ ይዘው የዕረፍት ቃልና መዝሙር የማያሰሙ አውደ ምህረቶችና አደባባዮችም ብዙ ናቸው፡፡ለዚህ ይመስላል በቀኝ ቆመናል እያልን በግራ ከምናስባቸው በሚበልጥ ክፋትና ነውር የተያዝነው፡፡ቦታ ቢያጸድቅ አዳም ከገነት የተሻለ የትም ሥፍራ አያገኝም፡፡

Monday, 31 March 2014

መልካም አገልጋይ ማን ነው ?


    ሳያነቡ የሚመረምሩ ፤ ሳይመረምሩ የሚተቹ ፤ በልማድ እውቀት የሚመላለሱ ፤ በደቦ ለስድብና ለድብደባ የሚጠራሩ ፤ ሳያምኑ የሚመሰክሩ ፤ በክርስቶስ ማዳንና ወንጌል ላይ  እልፍ አማራጭ የሚያኖሩ፤  ከልባቸው ሳይሆኑ አሜን የሚሉ፤ “ስለብልጥግና  ወንጌል” የፀጋውን ወንጌል የሚክዱ፤ እንኳን  ሳያዩ እያዩ እያነበቡ እየሰሙ የማያምኑ፤ በመልካም መሸነፍን  በባርነት  እንደመገት ጠልተው በክፉ  የሚሸንፉ፤ ስለእግዚአብሔር  መሳደብን  እንደፅድቅ  የሚቆጥሩትን ፤  “አንዳንዴ  በዋልድባም ይጨፍራል” በሚል ተረት  በእግዚአብሔር ጉባኤ በሥጋ አምሮት የሰከሩ … በእግዚአብሔር  አምልኮ ላይ እያመነዘሩ በአፋቸው ግን  እኔ ‹‹የጌታ መልካም ባርያ ነኝ›› የሚሉ  አማኞችን አይናችን ማየት ከጀመረ  ሰነባብቷል፡፡ 
    በፀሎት  ሳያጥሩ  የተዝረከረከ መታጠቂያቸውን  ጨብጠው   የሚቸኩሉ ፤  የእዩልኝና  ስሙልኝ  ድምፀትና ፉጨጽ ለማሠማት የሚንቀለቀሉ፤ በንግድ ብልሐት ካሴትና መፃህፍቱን  የሚሽጡ  ‹‹መንፈሳዊያን ነጋዴዎችን››፣ የደመቀ  መድረክና ኪስ የሚያሞቅ በጀትና አበል ያለበት እንጂ ለአንድ ነፍስ የማይገዳቸው ወሮ በል አገልጋዮችን፤ በህዝብ ጫንቃ እየኖሩ በህዝብ ላይ የሚቀማጠሉ፤ ፍትፍት ጎርሰው ምርቅ ስብከታቸውን የሚሰንጉ ፤ ድኃ ሲያዩ ቀሚሳቸውን ሰብሰብ አድርገው ፊታቸውን  አጨልመው  የሚራመዱ ባዕለጠጋ ሲያዩ  ደግሞ ቀሚሳቸውን  አንዘርፈው ጌታዋን እንዳየች ውሻ የሚቅበጠበጡ፤ ባዕለጠጋና  እግዚአብሔር  የተምታታባቸው… ስለገንዘብና  ክብራቸው ወንጌል የሚሸቃቅጡ ……  ከአፋቸው ግን ‹‹እኔ የጌታ አገልጋይ ባርያ ነኝ›› የሚሉ ለቁጥር  የሚታክቱ  አገልጋይ ካህናት ፤ ዲያቆናት፤  ሰባክያን፤ ዘማርያንን … እያየን ያላረርን ያልከሰልን ጥቂት አይደለንም፡፡
      ደቀ መዛሙርት በጻፉት መልዕክታት መግቢያ ላይ ራሳቸውን ‹‹የኢየሱስ ክርስቶስ ባርያ›› ብለው አስቀምጠዋል፡፡(ሮሜ.1÷1፤ፊሊ.1÷1፤ቲቶ1÷1፤2ጴጥ.1÷1፤ያዕ.1÷1፤ይሁ.1÷1)፡፡ባርያ የሚለው ቃል በግሪኩ ሁለት ትርጉሞች ያሉት ነው፡፡

Thursday, 27 March 2014

ጌታ መኖርያህ ነው!



በእድሜ ስልቻ በዘመን ቀልቀሎ
ማቱሳላ ኖረ ምንም ተሸክሞ?!
የቀደመው ጸጋ ዕድሜ ካስቆጠረ

Monday, 24 March 2014

ጸሎት - አሜን ሆይ በቶሎ ናልን! (ራዕ 22፣ 20)



    በቀደመው ብሉይ ኪዳን  ልጄ ወዳጄን እልክላችኋለሁ፤ መጥቶም ሰዎችን ሁሉ ከኃጢአታቸው ሁሉ በፀጋው ያድናቸዋል ብለህ ኪዳን ሠጥተህ እንደኪዳንህ ቃልህ ያልታበለ አብ አባት ሆይ ስግደት፤ አምልኮ ፤ሽብሸባ፤ ዝማሬ ፤ እልልታና ውዳሴ ከፍጥረት ሁሉ ተጠቅልሎ ለገነነው ድንቅ ስምህ ይሁን፡፡
    አቤቱ ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ አንተ የፍጥረት ሁሉ ናፍቆት፤ “ያልተሠራ ልብስ ፤ ያልተፈተለ ቀሚስ ፤ ወደአባቱ ለመድረስ ጎዳና ፤ ወደወለደው ለመግባት የሚሆን በር እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው”  (ቅዳሴ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ) የተባለልህ መድኃኒታችንና ቤዛችን ሆይ እንዳንተ የሆነልን፤ ዋጋ ላልነበረን ዋጋችን ሆነኸን፤በሰማይና በምድር አግነህ ተወዳጆች ላደረገን፤ ወንድምና አባታችን ሆይ አንተን የምናመሰግንበት ብዕርና ቃል ገና አልተፈጠረምና በአርምሞና  በተመስጦ ምስጋናችንን በመንፈስ በበገና ቅኔ እንደረድርልሐለን፡፡
    መዳናችንን ያስታወቅኸን፤ ልጅነታችንን ለመንፈሳችን የመሰከርክልን፤ የክርስቶስን የመስቀል ሥራ በልባችን ፅላት ላይ የቀረፅክልንና እናየውም ዘንድ የረዳኸን፤ በሐዘናችንንና በስብራታችን ሁሉ ያፅናናኸን ወጌሻ ሆነህ የዳስስከን ማህየዊ መንፈስ ቅዱስ ሆይ ለፍጥረት አለቆችና ለምድር መላዕክት የሰጠነውን ስግደትና ምስጋና ውዳሴና ቅዳሴ ክብርና አምልኮ ነጥቀን ጰራቅሊጦስ ለምትሆን ላንተ፤ ለሥላሴ መንግስት ባለመታከት እናቀርባለን፡፡ አሜን፡፡
    አቤቱ ሆይ ! ጎረቤትነት በቂም መርዝ ተመርዟል፤ባልንጀርነት በሐሜትና በክህደት ተፈቷል፤  ወንድማማችነት በዕላቂ ገንዘብና በውርስ እዳሪ ደም ተቃብቷል፤ ቅስናው ልማድ፤ ድቁናው ወግ፤ ጵጵስናው ሹመት (ሺህ-ሞት) እንጂ ለመንጋህ መራራትን አላስተማረንምና፤ ሐሰት እንጂ እውነት ከክብሯ ተራቁታ ዕርቃንዋን ቀርታለችና…….. አቤቱ ጨርሰን ሳንጠፋ ናልን!

Tuesday, 18 March 2014

ግብረ ሰዶማዊነት - የዘመናችን መጻጉዕ (የመጨረሻ ክፍል)


Please read in PDF

    አንድ የምወደው ባልንጀራ ወዳጅ ዳኛ አለኝ፡፡ለብርቱ ጉዳይ እንደሚፈልገኝ በስልክ አቻኩሎ ጠራኝ፡፡አላመነታሁም … ከተሰየመው ችሎት ገብቼ አንድ ጉዳይ እንድሰማ ጋበዘኝ፡፡የአርባ ሁለት አመት ጎልማሳ የስድስት አመት ወንድ ህጻን በፈጸመበት ግብረ ሰዶማዊነት መቀመጥ እንደማይችል ብሎም በፊንጢጣ መቀደድ እንደሚሰቃይ ከውሳኔው ስሰማ ረዥም ዝምታ ከችሎቱ በኋላ ወደ ውስጤ ተሰማኝ፡፡(አቤቱ ይህን ሁሉ ለምን ታሳየኛለህ? ... ጥፋትና ርኩሰት መዋረድስ በመካከላችን ስለምን ሆነ?  … አቤቱ ምድሪቱ ለክፉዎች ተሰጥታለችና ጨርሶ ሳይጨልም ድረስልን!!!...የሚያቃጥል እንባ … መንፈስን የሚለበልብ የቁጣ ነበልባል … )
     መንግስት “ከብዙ ነገር አንጻር” ግብረ ሰዶማዊነትን በግልጥ ባይቃወምም በዝምታ ሊደግፍ እንደሚችል ታዝበናል፡፡ ቢያንስ እንደአሸን እየፈሉ የመጡትን እኒህን የሰዶም ሰዎች ሊያስተምር በሚችል መልኩ እንደወንጀል ህጉ ቀጥቶ አለማሳየትና አቀንቃኞቹን አለመግራት በግልጥ ከመደገፍ አይተናነስም፡፡ ከሁሉ በላይ ግን ቤተ ክርስቲያን ለዚህ ነገር ትኩረት ሰጥታ አለመስራቷ ይበልጥ እጅግ የሚያደማ ነገር ነው፡፡ በተለይ በገዳም ባሉ ጥቂት በማይባሉ መነኮሳትና መነኮሳይያት ዘንድ ከሚሰሙ ነውሮች መካከል አንዱ ግብረ ሰዶማዊነት ነው፡፡ምናልባት እንዲህ ደፍሬ የምናገረው የቤተ ክርስቲያንን ነውር መግለጥ የሚያስደስት ሆኖ አይደለም፡፡ነገር ግን ማንቀላፋታችን አለልክ ስለበዛ ፣ይህ ነውር ሩቅ እንጂ እዚህ አፍንጫችን ሥር ያለ ስላልመሰለንና ጣታችንን በሌሎች እየቀሰርን የንስሐ ዘመናችንን በክስና በሽንገላ እየጨረስነው እንደሆነ ስለታየኝ ነው፡፡የማንክደው እውነት ግብረ ሰዶማዊነት በመካከላችን አለ፡፡መኖር ብቻ ሳይሆን ቁጥሩ ቢያንስም እንደሐገሪቱ ህግ የተቀጡና በማረሚያ ቤቶች ያሉ ሰዎችም አሉ፡፡

Sunday, 16 March 2014

ግብረ ሰዶማዊነት - የዘመናችን መጻጉዕ(ክፍል -1)


Please Read in PDF    
  
አንድ ማታ ስልኬ ምሽት አራት ሰዓት ገደማ ጮኸች፡፡ለማንሳት እያቅማማሁ ስልኬን አነሳሁት፡፡ “Hello” የሚለውን ቃል ከአንደበቴ ከማውጣቴ ተጨንቆ የሚያለቅስ የወንድ ልጅ የሲቃ ድምጽ ወደጆሮዬ አቃጨለ፡፡“ወንድ ልጅ ሳይሸነፍ እንዲህ እንደማይሆን” ውስጤ ሊደመደም አልዘገየም፡፡ከብዙ የማጽናናት ቃል በኋላ “ማታ ማታ ድቁና እናጠና ሳለን አንድ ወንድም በተለያየ ጊዜ ሲነካካኝ በወንድማዊ ፍቅር አስቤ ዝም አልኩት፡፡በሌላ ቀን ግን በጣም አጥንተን ደክሞኝ ስለተኛሁ ፈጸመብኝ፡፡ከዚያ ቀን በኋላ ሲደጋገምብኝ ከእርሱ ጋር ብቻ ሳይሆን እኔም ከሌላ ሰው ጋር ለመፈጸም ተነሳሳሁ፡፡እናም አንድ ቀን ሌላ ወንድሜን እየነካከሁት ሳለ ያልጠበቅሁት ቁጣ አገኘኝ፡፡ “ባልመለስ ለቤተሰቤም እንደሚናገር አስጠነቀቀኝ፡፡እናም ቀኑን ሙሉ ሳለቅስ ነው የዋልኩት፡፡ቢጨንቀኝ አንተ ጋ ደወልኩኝ፡፡እባክህን ምከረኝ፡፡ምን ላድርግ? … ”
      ብዙ የሚያለቅሱ አይኖች ፣መታበስ የሚፈልጉ የእንባ ዘለላዎችን አሰብሁ፡፡እናም ውስጤን አንዳች ነገር ሲንጠኝ ታወቀኝ፡፡ለአፍታ በመካከላችን ዝምታ ሆነ፡፡ይበልጥ እንዳይጨንቀው ፈርቼ “የእግዚአብሔርን ምህረትና ይቅርታ፤የሰውንም ልጅ ኃጢአተኝነት” አወራለት ገባሁ፡፡ዛሬ በእግዚአብሔር ጉልበት ይህ ወንድም ተመልሶ በቤቱ አለ፡፡
     ብዙ ጊዜ በተለያየ መንገድ ከሚደርሱኝ አስተያየቶች ትልቁን ስፍራ የሚይዙት “ጽሑፎችህ በጥናታዊ ይዘት ተደግፈው ስለማይቀርቡ የመረጃ እጥረት ይታይባቸዋል፤ ከወሬም ያላለፉ ናቸው” የሚለው ነው፡፡ የሚያሳዝነው ነገር ኃጢአትን በተመለከተ ምን አይነት ጥናት ቢካሄድ እንደሚወዱ አልገባኝም፡፡እውነት እንናገር ከተባለ ቅዱስ ጳውሎስ የቆሮንቶስን ቤተ ክርስቲያን “በአጭር ቃል በእናንተ መካከል ዝሙት እንዳለ ይወራል የዚያም ዓይነት ዝሙት በአሕዛብስ እንኳ የማይገኝ ነው፥ የአባቱን ሚስት ያገባ ሰው ይኖራልና።”(1ቆሮ.5÷1) በማለት ሲናገር ከሰማው ነገር ተነስቶ እንጂ ምንም ስለኃጢአት በሰራው ጥናታዊ ጽሁፍ አይደለም፡፡ምነው ጥናታዊ ጽሁፍን ለኃጢአት ከማሰብ ለሌላ ነገር ብናውለውስ?

Monday, 10 March 2014

ምኩራብ



ቅዱስ ያሬድ የጌታን ጾም ሳምንታት በሠየመበት ስያሜው ሦስተኛውን ሳምንት ምኩራብ ብሎ ሰይሞታል፡፡ጌታ በምኩራብ ማስተማሩን፤መስበኩንና መፈወሱን ለማስታወስ፡፡ምኩራብ የእስራኤል ልጆች ወደባቢሎን በንጉስ ናቡከደነጾር በተማረኩ ጊዜ ጎበዛዝት ተግዘው፤ኢየሩሳሌም ባድማ ሆና መቅደሷም ፈርሶ ተፈታ በነበረችበት ወቅት በባዕድ ምድር እግዚአብሔርን ለማምለክ የሰሩት የአምልኮ ሥፍራ ነው፡፡የሄዱባት ባቢሎን ጣኦትና ቤተ ጣኦት እንጂ እግዚአብሔርና ቤተ መቅደስ አልነበሩባትምና አይሁድ የእግዚአብሔርን ፊት ለመፈለግ ፣ቃሉን ለማጥናትና ለጸሎት እንዲያመቻቸው በየሥፍራው ምኩራብን መሥራት ጀመሩ፡፡
   የእስራኤል ልጆች ከባቢሎን ምርኮ ተመልሰው ወደደሀገራቸው በተመለሱ ጊዜም ከመቅደሱ ጎን ለጎን ምኩራብን ሠሩ፡፡ምኩራብ በጌታ ዘመን ለአይሁድ ዋነኛ የአምልኮ ሥፍራ በመሆኑ ቅዱሳት መጻህፍትን በውስጡ በማከማቸት ፣ድምጻቸውን ከፍ አድርገው በማንበብና በመተርጎም እንዲሁም እግዚአብሔርን ማምለክ የሚያዘወትሩበት ሥፍራ ሆነ፡፡
    በአንድ ሥፍራ ላይ ከሰባት እስከአስር ብዛት ያላቸው አባወራዎች ካሉ ምኩራብን እንዲሰሩ ይፈቀድላቸዋል፡፡ዋና አላማው በአንድ ሥፍራ ያሉ ወገኖች በቅርብ በመገናኘት ቅዱሳት መጻህፍትን እንዲያጠኑና እግዚአብሔርን እንዲያመልኩ ማድረግ ነው፡፡ የምኩራቡ አገልጋይም ዋና ሥራው ልጆችን ማስተማር፣ የቅዱሳት መጻህፍትን ጥቅልሎች ማቅረብ ፣ሌሎችንም ሥራዎችን መስራት ነው፡፡(ሉቃ.4÷20)
    አገልግሎቱ ስለማቋረጥና ብዙ ምኩራቦችም ስለነበሩ(ሐዋ.9÷2፤13÷3)በየቀኑና በየሰንበቱ ህዝቡ ሁሉ በአቅራቢያው ወዳሉት ምኩራቦች ይሰበሰብ ነበር፡፡(ሐዋ.13÷14፤17÷17)፡፡ የሚሰበሰቡት ሁልጊዜም ከላይ  ለሠፈረው ዓላማ ብቻ ነው፡፡ ምኩራብ ከመቅደስ ያነሰ መስዋዕት የማይቀርብበት የአምልኮ ሥፍራ ነው፡፡ጥቂት አባወራዎችና መንገደኞችም ጎራ እያሉ ቃሉን በማጥናት እግዚአብሔርን የመፍራት ጥበብ ይማሩበታል፡፡