የጌታ ጾም መታሰቢያ የመጨረሻው ሳምንት ስያሜ ሰሙነ ሕማማት ይባላል፡፡
በዚህ ሳምንት ከምን ጊዜውም በላይ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአይሁድ “ወገኖቹ” የደረሰበት ጸዋተወ መከራ ከወንጌላት፣
ከግብረ ሕማማትና ከሌሎችም መጻሕፍት እየተውጣጡ ይነበባሉ፤ ሕማማቱንም ማዕከል ያደረጉ ሥርዓተ አምልኮዎች በጸሎት፣ በዝማሬ፣ በንባብና
በቅዳሴ ይቀርባሉ፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ የጌታን ሕማም የጌታ እራት በቀረበበት ጊዜ መናገርና መመስከር
እንዳለብን “ይህን እንጀራ በበላችሁ ጊዜ ሁሉ፥ ይህንም ጽዋ በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ሞቱን ትናገራላችሁና፤”
(1ቆሮ.11፥26) በማለት ይናገራል፡፡ ጌታ ኢየሱስም ከሙታን መካከል ከተነሣ በኋላ ደቀ መዛሙርቱን፣ “እርሱም፦ ከእናንተ ጋር
ሳለሁ በሙሴ ሕግና በነቢያት በመዝሙራትም ስለ እኔ የተጻፈው ሁሉ ይፈጸም ዘንድ ይገባል ብዬ የነገርኋችሁ ቃሌ ይህ ነው አላቸው፡፡
በዚያን ጊዜም መጻሕፍትን ያስተውሉ ዘንድ አእምሮአቸውን ከፈተላቸው፤ እንዲህም አላቸው፦ ክርስቶስ መከራ ይቀበላል በሦስተኛውም ቀን
ከሙታን ይነሣል፥” (ሉቃ.24፥46) አላቸው፡፡
