Monday, 10 July 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ ሦስት)

Please read in PDf
3.    ይጣን፦ ብዙ ስሞች ያሉት ያሉት ሲሆን፣ ሰይጣን በዕብራይስጡ አሰናካይ፣ ስም አጥፊ፤ (ኢዮ.1፥6 ፤ ዘካ.3፥1 ፤ ማቴ.4፥10 ፤ ራእ.12፥9)፤ ዲያብሎስ ደግሞ ስም አጥፊ፣ ከሳሽ፤ ቤልሆር ማለት ደግሞ የማይረባ ከንቱ (2ቆሮ.6፥15)፤ አብዶንና አጶልዮንም አጥፊ (ራእ.9፥11) ተብሏል፤ በሌላ ሥፍራ ደግሞ የዚህ ዓለም ገዥ(ዮሐ.12፥311)፣ ወይም የዚህ ዓለም አምላክ (2ቆሮ.4፥11) ተብሎ ተጠርቷል፡፡ በተለይም ደግሞ ስለተንኮለኛነቱና አታላይነቱ የቀደመው እባብ ወይም ታላቁ ዘንዶ(ራእ.12፥9)፣ ዛቻ ወዳጅና የሚያስፈራራ ስለመሆኑ ደግሞ “የሚያገሳ አንበሳ” ተብሏል፤ (1ጴጥ.5፥8)፡፡
     ሰይጣን ዋና ዓላማው ሰዎች ለጌታችን ኢየሱስ ያላቸውን ትኩረት ማስነፈግ ነው፡፡ ትኩረታቸውንና ፊታቸውን ከኢየሱስ ዘወር ባደረጉ ጊዜ ለማን እንደሚያደሉና ወደማን እንደሚያቀኑ በትክክል ያውቀዋል፡፡ ይህንንም ለማድረግ ስውር መረቡን ይዘረጋል፡፡ የክፋት መረቡንም ለመዘርጋት የሚራዱ ብዙ ኃይላትና ሠራዊት፣ ተባባሪዎችም አሉት፤ (ኤፌ.6፥10)፡፡ ከዚህም ባሻገር ልናጣጥልና ልንንቀው የማንችለው የክፋት ጥበብንም የተመላ ነው፡፡

Friday, 7 July 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (የመጨረሻ ክፍል)

Please read in PDF
እግዚአብሔር ዘፈንን አይባርክም!

    ከዘፋኞች በተደጋጋሚ የምናደምጠው፣ “እግዚአብሔር ዘፈናቸውን እንደሚባርክ፣ ለዘፈን የሚኾን ድምጽ እንደሰጣቸው፣ በመዝፈናቸው እግዚአብሔርም ጭምር ሊደሰት እንደሚችል፣ እንዲያውም ለመዝፈናቸውና ካሴት ለማሳተማቸው ጭምር እግዚአብሔር እንደረዳቸውና እንደባረከላቸው” ሳያፍሩ ሲናገሩ ይደመጣሉ፡፡ እኔን ብዙ ጊዜ እንደገባኝ ግን፣ “እግዚአብሔር” ሲሉ፣ ቅዱሱንና ለኃጢአት ልጁን አሳልፎ የሰጠውን እግዚአብሔርን፣ እግዚአብሔር ብለው እንደማይጠሩ በእርግጠኝነት መናገር እችላለሁ፡፡ ምክንያቱም በየትኛውም ዘመን ቅዱሱ እግዚአብሔር ከኃጢአት ጋር የተደራረደረበትና “ኃጢአትን የባረከበትን ሂደት” ሰምተንም፤ አይተንም አናውቅምና፤ ቅዱሳት መጻሕፍትም እንዲህ ያለውን ምስክርነት ፈጽመው አላስቀመጡልንም፡፡
     እግዚአብሔር ዘፈንን የሚባርክ ከሆነ፣ ከዘፈን ጋር የተጠቀሱትንም የሥጋ ፍሬዎች “ዝሙትን፥ ርኵሰትን፥ መዳራትን፥ ጣዖትን ማምለክን፥ ምዋርትን፥ ጥልን፥ ክርክርን፥ ቅንዓትን፥ ቁጣን፥ አድመኛነትን፥ መለያየትን፥ መናፍቅነትን፥ ምቀኝነትን፥ መግደልን፥ ስካርን፥ … ይህንም የሚመስለውን ሁሉ” መባረክ አለበት እያልን ነው፡፡ ሌላውን ሁሉ ጥሎ፣ ነጥሎ ዘፈንን ይባርካል ማለት፣ እግዚአብሔርን የስንፍና ሃሳባቸው ደጋፊ ለማድረግ ከማሰብ የመነጨ ተላላነት ነው፡፡ እንጂማ ዘፈን ከምንና ከማን ጋር እንደተጠቀሰ በትክክል ቢያነቡት፣ “እግዚአብሔር ዘፈንንም ይባርካል” በማለት እግዚአብሔር ላይ ለመሳለቅ ባልደፈሩ ነበር፡፡

Thursday, 29 June 2017

“እኔ” ሥልጣን ይጣ!

አርነት አታውጣኝ ለሥጋ ፈቃዴ፣
ነጻነት አትስጠኝ እንድሆን መደዴ፤
የቃልህን ብርሃን በዝቶልኝ ካየሁህ፣

Friday, 23 June 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ ሁለት)

Please read in PDF

2.    ኃጢአት፦ በዕብራይስጥ [ኀቻታ] በግሪክ ደግሞ [ሐማርቲያ] ተብሎ የተነገረ ቃል ሲሆን፣  በተካካይ የአማርኛ ትርጉሙ ደግሞ “ዒላማን መሳት” ተብሎ ተተርጉሟል፡፡ ይኸውም እግዚአብሔር እንድንደርስበት የሚፈልገው ዋና ዒላማና ግብ አለ፡፡ እዚያ እርሱ ካሰበበት መድረስ አለመቻል ዒላማን መሳትና ኃጢአት ነው፡፡
     የእግዚአብሔር ልጆች ዋና ዒላማችን እግዚአብሔር ራሱ ነው፤ ከእርሱ ፈቀቅ ማለት ቀስትን እንደሚስት ዒላማ ሳች (መሳ.20፥16)፣ እግሩን በማፍጠን ከእውነት መንገድ ይስታል፤ (ምሳ.19፥2)፡፡ በማንኛውም ሁኔታ ከእግዚአብሔር ያነሰ ዒላማ፣ ከእርሱ ያነሰ ግብም ሊኖረን አይገባም፡፡ ከእግዚአብሔር ያነሰ ዒላማ ካለን ግን፣ ያ የያዝነው ዒላማ መልካምም ቢሆን እንኳ ኃጢአት ነው፡፡

Sunday, 18 June 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (ክፍል 5)

Please read in PDF
በቋንቋው ተናጋሪ ሊቃውንት[1] ዘንድ ዘፈን ኃጢአት ነው!
      አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም ሆነ ደስታ ተክለ ወልድም የዘፈንና የዘፋኝነትን ዓለማዊነት ወይም ኀጢአትነት በግልጥ አስቀምጠዋል፡፡ በመጽሐፎቻቸውም በግልጥ ቃል፦ “ዘፊን፤ ኖት፤ (ዘፈን ይዘፍን ይዝፍን፡፡ ዐረብ)፤ መዝፈን መወዛወዝ፤ ማሸብሸብ ማጋፈት መዝለል መፈንጨት፡፡ … ዘፋኒ፤ (ኒት፤ ንያን፤ ያት)፤ የሚዘፍን ዘፋኝ፤ ተወዛዋዥ፡፡ ዘፈን፤(ናት)፤ በቁሙ ዝላይ እስክታ፡፡”[2]
    የደስታ ክለ ወልድ መዝገበ ቃላትም “ዘፈን”[3] የሚለውን፣ “ዘፈን፤ (ዘፊን ዘፈነ)፤ ቀነቀነ አወረደ ግጥም ገጠመ፣ አዜመ፣ አንጐራጐረ፣ ዘለለ፣ ተውረገረገ፡፡” አሁንም ዘፈነ፤ ተንቀጠቀጠ ተንዘፈዘፈ፡፡ ዘፋኝ(ኞች)፤ የዘፈነ የሚዘፍን፤ አውራጅ አንጐራጓሪ ዘፈን ወዳድ(መዝ.፹፯፥፯)” በማለት ሲያስቀምጡት፣ ገላ.5፥21 ላይ የተቀመጠውን ዘፋኝነት የሚለውን ሃሳብ ደግሞ፣ “መጽሐፍ ግን መሶልሶል[4][ሶለሶለ - አንሶለሶለ፣ አዞር፣ አንቀዠቀዠ፣ አንቀለቀለ መንሶልሶል፣ መዞር፣ መንቀዥቀዥ] ይላል” በማለት ጥቅሱን ጠቅሰው አስቀምጠውታል፡፡
   ሰርጸ፣ ሽምጥጥ አድርጎ “የመጽሐፍ ቅዱስ መተርጉማን ሌላ ስያሜ ስላጡለት ዘፈን አሉ እንጂ ዘፈን መባል አይገባውም” የሚል ጽኑ አቋሙን ደጋግሞ አስተጋብቷል፡፡ ምናልባት ይህንን ሲል ሁሉን አዋቂ ነገር ጠንቃቂ ወደመሆን የተጠጋ ሳይመስለው፤ እንደሆነ ሳያስብ አልቀረም፡፡ ነገር ግን የእርሱን ሃሳብ መተርጉማኑም ሆኑ የቋንቋው ሊቃውንት ሲደግፉት ፈጽሞ አይታይም፡፡

Wednesday, 14 June 2017

አታወሳስቡብን!

ውስብስብ አይደለም ያልተብራራ ቅኔ
ለእርሱ እንደተገባሁ ኃጢአተኛው እኔ፤
ለብዙ ኃጢአቴ እልፍ ምሕረት ፈሶ

Sunday, 11 June 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ አንድ)

Please read in PDf
የምንዋጋው ከማን ጋር ነው?
    በአጭር ቃል፣ የየራሳችንን ሰባኪና ማኅበር፣ ዘማሪና መጋቢ፣ የሐሰት አጥማቂዎችን፣ የነቢያትና “መፍትሔ አምጪ ነን” ባይ የሆኑ የመጋብያን ትንቢተኞችን  … ቃል ከኢየሱስ ጌታችን ቃል ይልቅ በማድመጥና በመከተል ስተናል፡፡ ልክ እንዲሁ ከማን ጋር እንደምንዋጋ አለማወቃችን ከደካማው ፍጡር ጋር በመታገል ዘመናችንን እንድንጨርሰው አድርጐናል፤ መጽሐፍ ቅዱስ ከማን ጋር እንደምንዋጋ፥ “መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ፤” (ኤፌ.6፥12) በማለት ገልጦታል፡፡

Thursday, 8 June 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥር)

Please read in PDF
5.  ውነተኛ ወታደር በማናቸውም የራሱ እቅድና ዝግጅት ቢኖረውም ዘወትር ግን ወደየትኛውም አቅጣጫ መሄድና ማናቸውንም ሥራዎች ለመሥራት ዝግጁ ነው፡፡ እውነተኛ ክርስቲያንም የራሱ የሆኑና በግሉ የሚሠራቸው ብዙ መልካም ነገሮች ሊኖሩት ይችላሉ፤ ነገር ግን በክርስትና ሕይወት ጉዞው ቀዳሚውና ዋናው የሚኖርለት የክርስቶስ ነገር ሊሆን ይገባዋል፡፡
      ክርስቲያኖች ከክርስቶስ ላነሰ ኑሮ ልንኖር አልተጠራንም፡፡ ክርስቲያን ከእርሱ ላነሰ ኑሮ የሚኖር ከሆነ ከሁሉ ይልቅ ምስኪን ነው፡፡ የክርስቶስ የሆኑቱ ታማኞቹ ደቀ መዛሙርት፣ “በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮች” (ሐዋ.1፥8) የሆኑት፣ ለየትኛውም ለጌታችን ኢየሱስ ሥራ ዝግጁና በማናቸውም አቅጣጫ ቢሄዱ በደስታ በመታዘዝ ነበር፡፡ ለየትኛውም አገልግሎትና ለኢየሱስ ጌታችን ሥራ የጨከነና የበረታ ልብና መንፈስ ነበራቸው፡፡

Saturday, 3 June 2017

ሙሽሪትን ሊያስውብ

ክርስቶስ በሞቱ በደሙ ያቆማትን
ከፊት መጨማደድ ሊያጠራና “ሊያድን”
አዲስ ማኅበረሰብ አዲስ ልዩ ትውልድ

Thursday, 1 June 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (ክፍል 4)

Please read in PDF

የቤተ ክርስቲያን አባቶችም ዘፈንን በኀጢአትነቱ ገልጠዋል፤

   የቤተ ክርስቲያን አባቶች ስንል እንዲሁ ከምንም ነገር ተነስተን አይደለም፡፡ እኒህ አባቶች ለእውነተኛው የክርስትና ትምህርት በመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ላይ ቆመው ዋጋ የከፈሉ በመሆናቸውና ለመጽሐፍ ቅዱስ እውነት “በመሟገታቸው” ነው፡፡ ትምህርቶቻቸው፣ ምክሮቻቸው፣ ተግሳጾቻቸው ብቻ ያይደለ የሕይወታቸውም ቅድስና ጭምር የተመሰከረላቸው፣ የእግዚአብሔርን ሉዓላዊነትና የመጽሐፍ ቅዱስን ሥልጣን አምነው የተቀበሉና በዚህም መሠረትነት ላይ ቆመው የጻፉ መሆናቸውን በመመዘን የምንቀበላቸው ናቸው፡፡
   ከእነዚሀ ቅዱሳን አባቶች መካከል ዘፈንን በግልጥ የተቃወመውና እንድንርቀው ያስተማረን አባት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ነው፡፡  ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በተግሳጹ እንዲህ አለ፣ “ስለዚህ … ዘፈንን ትተዉ ዘንድ እማልዳችኋለሁ፡፡ ኀላፊ የሚሆን ፈቃደ ሥጋን ተዉት ብዬ እማልዳችኋለሁ፡፡ ሲዘፍኑ ላደሩት ጧት ለዋሉት ማታ መሸታ መግዛትን ተው ብዬ እማልዳችኋለሁ፡፡”[1] “ዳግመኛም ሲሰስን እንዳየኸው ጋሬዳ፤ ዘፈን፤ ጨዋታ፤ መሸታ ወዳለበት ሲሔድ ብታየው፡፡ ይህንንም ይተው ዘንድ መላልሰህ ማልደው፡፡”[2]

Wednesday, 24 May 2017

አርጓል በክብር

መቃብሩን በድንጋይ በማኅተም ቢያትሙ
አልተነሣም ብለው በገንዘብ ቢስማሙ

Tuesday, 23 May 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል ዘጠኝ)

Please read in PDF
3.     ከራን ተቀባይ ነው“እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎ ወታደር ሆነህ፥ አብረኸኝ መከራ ተቀበል” (2ጢሞ.2፥3)፡፡ የእውነተኛ አማኝም ሆነ አገልጋይ ዋና መገለጫው፣ ከጠላት ዘንድ የሚመጣበት ብርቱ ሰልፍና ዋና ተቃውሞ ነው፡፡ ክርስቲያንን ከዓለም ጋር የሚያስማማው ምንም የሕይወት ዘይቤ ወይም ሥርዓት የለውም፡፡ ጌታ ራሱም፣ “በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ” (ዮሐ.16፥32) በማለት መከራው የማይቀርና ነገር ግን አሸናፊው ቀድሞ መከራውን ስላሸነፈው ፍርሃት እንደማይገባ አስረግጦ ነግሮናል፡፡ ዓለም ስለእኛ የምትመሰክረው “በጎ ነገር” ካላት፣ ክርስትናችንን ቆም ብለን መፈተሽ ይገባናል፡፡
    ቅዱስ ጢሞቴዎስ በኋለኛው ዘመኑ በመከራው ጽናትና እየሆነ ባለው ነገር ፈጽሞ በፍርሃት ተውጦ ነበር፡፡ ስለዚህም ከመከራው ጽናት የተነሣ መንፈሳዊ ድፍረትን አጥቶ ነበር፤ (2ጢሞ.1፥7)፡፡  በመፍራትም ወደኋላ እንዳይል አበክሮ ቅዱስ ጳውሎስ ያበረታታዋል፡፡ እምነታችንም፤ አገልግሎታችንም በክርስቶስ ጸጋ ላይ የተመሠረተ ነው፤ ደግሞም ይህን ብርቱ ሥራ መከራ በመቀበል ልናምነውና ልናገለግለው ይገባናል፡፡ ውጊያችንም ሁሉ ታላቅ ወታደራዊ ጽናትን በሚጠይቅ ማንነት ውስጥ ማለፍ ይገባናል፡፡

Friday, 19 May 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (ክፍል 3)

Please read in PDF

ዘፈን ራሱ ኮሞስ ነው!

    ዘፈን የሚለውን ሃሳብ አስቀድመን ስንተረጉም፣
1.      በጥንት ግሪክ ለወይን አምላክ በሚደረግ ታላቅ ግብር ላይ ተሰልፎ መዞር፣ መፈንደቅ፣ መጨፈር፣ መጯጯኽ፣ መፈንጠዝ፣ ኢ ሥነ ምግባራዊና ገደብ የለሽ በኾነ የአልኮል መጠጥና ገደብ የለሽ በኾነ የአልኮል መጠጥና በምግባረ ብልሹነት እርካታ ለማግኘት የሚደረግ ወሲባዊ ጭፈራ( ... Drinking parties involving unrestrained indulgence in alcoholic beverages and accompanying immoral behaviour, - ‘orgy, revelling, carousing.)
2.     በአማልክት (በጣዖታት) ፊት በቡድንና በግል ሚደረግ ፈንጠዝያ፣ ዝሙትና መጠጥ ባካተተ መልኩ የሚደረግ ጭፈራ፣
3.     በቡድን በተደራጀ መልኩ በተለያየ ሁኔታ የሚደረግን አደባባያዊ ትርኢት መልክ ያለው የመንደር ክብር በዓል፣ ጭፈራ፣ ዘፈን፣ ግጥም፣ ዜማ፣ መሽከርከርን ... የሚያመለክት ትርጉም ያለው ነው፡፡”
ብለን በክፍል አንድ ላይ ማቅረባችንን መርሳት የለብንም፡፡
     እናም፣ ዘፈንን ኃጢአት ነው የምንለው “ዘፈን” የተባለውን “አንድ ቃል” አንጠልጥለን፤ እርሱኑ ደግሞ ለጥጠን አይደለም፡፡ ቀድሞ እንደተናገርነው የምንተረጉመውን ሁሉ የምንተረጉመው ለእግዚአብሔር ክብርና ለእኛ ጥቅም ነው፡፡ ከላይ በተለያየ ይዘት በትርጉም ከተጠቀሱት ውስጥ፣ ዝርዝር ሃሳብ እናውጣ ብንል፤ ዘፈን ማለት፦
1.     መንፈሳዊ አምልኮ ጋር መዛመድ የማይችል ርኩስ ጠባይን አመልካች ነው፡፡ በተለይም በጣዖታት ፊት የሚደረግ ማናቸውም የደስታ መግለጫ ሥርዓትን ማከናወን፣ “ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ” (ዘጸ.20፥3) የሚለውን ሕግ ለማስቃረን አሳላጭ መንገድ ስለሆነ፣ ዘፈን አደገኛነቱ ምንም አያጠያይቅም፡፡

Monday, 15 May 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (ክፍል 2)

Please read in PDF
በመጽሐፍ ቅዱስ “ዘፈን” የተገለጠበት አገላለጥ
   በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ፣ በተለይም በአማርኛው በተመሳሳይ ቃል ወይም ሐረግ ተጠቅሶ የተለያየ ፍቺ ያለው ቃል ብዙ ቦታ ይገኛል፡፡[1] ስለዚህ ቅዱሳት መጻሕፍትን ስናጠና የቃሉን መመሳሰል ሳይሆን ቃሉ ያለበትን ወይም የተነገረበትን ዓውድ በትክክል ማጥናትና መስተዋል ይገባናል፡፡ “ዘፈን”ም ለተለያየ ሃሳብ፤ በተለያየ ዓውድ ተነግሯል፡፡ እናም እንደየተነገረበት ዓውዱ የተለያየ ትርጉሞችና ሰፊ ሃሳቦችን ይዟል ማለት ነው፡፡ ጥቂቱን ብንመለከት እንኳ፦
1.    “ዘፈን” በቅዱስ አምልኮ ውስጥ ሲጠቀስ፤
    በብሉይ ኪዳን የእስራኤል ልጆች በዘፈን ለእግዚአብሔር መንፈሳዊ አምልኮን ያቀርቡ ነበር፡፡ የእስራኤል ልጆች ከግብጽ ምድር፤ ከባርነት ቤት ሲወጡ፣ ፈርዖንንና ሠረገላውን ሁሉ በባሕር አስጥሞ፣ ለእነርሱ ግን ሞገስንና ግርማን ሰጥቶ፣ የኤርትራን ባሕር በድል ሲሻገሩ በዝማሬ አመሰገኑ፤ (ዘጸ.15፥1)፡፡ በሌላ ሥፍራ፣ “ዳዊትም በሙሉ ኃይሉ በእግዚአብሔር ፊት ይዘፍን ነበር፤ ዳዊትም የበፍታ ኤፉድ ለብሶ ነበር፤ … የእግዚአብሔርም ታቦት ወደ ዳዊት ከተማ በገባ ጊዜ የሳኦል ልጅ ሜልኮል በመስኮት ሆና ተመለከተች፥ ንጉሡም ዳዊት በእግዚአብሔር ፊት ሲዘልልና ሲዘፍን አየች፤ በልብዋም ናቀችው፡፡ … በእግዚአብሔር ፊት ዘፍኛለሁ፤ በእግዚአብሔር ሕዝብ በእስራኤል ላይ አለቃ እሆን ዘንድ ከአባትሽና ከቤቱ ሁሉ ይልቅ የመረጠኝ እግዚአብሔር የተባረከ ይሁን ስለዚህም በእግዚአብሔር ፊት እጫወታለሁ፤” (2ሳሙ.6፥14-16 ፤ 21) በማለት ራሱም ገልጦታል፡፡

Wednesday, 3 May 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (ክፍል 1)

Please read in PDF
ሰርጸ ፍሬ ስብሐት[1] ሆይ! ቃሉን ለራስህ ሃሳብ አትጠምዝዘው!
መግቢያ
    በአንድ ሰሞን “ኦርቶክሳዊ ተብሎ ባለመጠራቱና የሌላ ቤተ እምነት ተከታይ ሆኗል ተብሎ መጠርጠሩ ያናደደውን ዘፋኝ” ተመልክቼ፣ “ዘፋኝ ለኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ምኗ ነው?” ብዬ ሃሳቤን ማፍሰሴ የሚዘነጋችሁ አይደለም፤ በዚያን ሰሞንና ከዚያም በኋላ ዘፋኙን “በመገሰጼ” የበዙ ተቃውሞዎች ገጥመውኝ ነበር፤ ተቃውሞዎቹ ሁለት መልክ አላቸው፤ አንዳንዶች የሌላውን[የዘፋኝን] ኃጢአት የምታወራው አንተ ማን ነህ? የሚሉ ሲሆኑ፣ ሌሎች ደግሞ ዘፈን ያልተከለከለ መሆኑን፣ ሥራ(ሙያ) መሆኑን፣ “እግዚአብሔር የሚባርከው” መሆኑን፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ራሱ የተጠቀሰ መሆኑንና ዳዊት መዝፈኑን፣ “እግዚአብሔርን በዘፈን አመስግኑት” መባሉን፣ ብሎም መኃልይ መኃልይ ዘሰሎሞን ስለ“ተቃራኒ ጾታ” ግንኙነት ካወራ፣ እኛስ ምናለ እንዲያ ብናደርግ የሚል “ሙግት” መልክ ሊያቀርቡልኝ ብዙ ጥረዋል፡፡ በአብዛኛው ግን ስድብ መልክ ስለነበረው አያንጽም፣ ሰውንም አያስተምርም ያልኩትን ሁሉ ለራሴ ከማንበብ፣ ሰዎችም እንዳይመለከቱት በማድረግ ወደቅርጫት እንዲጣል አድርጌዋለሁ፡፡ በዚህም ምክንያት ስለዘፈን አስፍቼ ለመጻፍ ከብዙ ጊዜ በፊት አስብ፤ አሰላስል ነበር፡፡
     ለዚህ ጽሁፍ ሌላው መነሻ ምክንያት የሆነኝ፣ በጄ ቲቪ የቴሌቪዥን ጣቢያ ሰኞ በ16/8/09 እና 23/8/09[2] ምሽት አራት ሰዓት ገደማ በሚተላለፈው የ“ብራና” ፕሮግራም ላይ፣ ሰርጸ ፍሬ ስብሐት የተባለ ሰው ሙዚቃን(ዘፈንን) በተመለከተ አንድ “ጥናታዊ ጽሁፍ”፣ በአንድ ሌላ ቦታ ላይ አቅርቦ የነበረውን ሲያስተላልፍ ያሳያል፤ ለሰርጸ “ጥናታዊ ጽሁፍ” መነሾ ምክንያቱ ደግሞ፣ ዮናስ ጎርፌ የተባለ ሌላ ሰው ቤት ያጣው ቤተኛ- ሙዚቃ፣ ሙዚቀኛነትና ኢትዮጵያዊቷ ቤተ ክርስቲያን በሚል ዘፈንን[ሙዚቃን] ባስመለከተ በጻፈው መጽሐፍ ላይ የቀረበ ነው፡፡ ዮናስ ጎርፌ ለተባለው ሰው በወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ዓቃቤ እምነት ላይ የሚሠሩ ብዙዎች መልስን ስለሰጡት እርሱን ማንሳት አልፈልግም፡፡ ሰርጸ ግን፣ “ቤት ያጣ ቤተኛ” መጽሐፍን፣ “ከዚያኛው ቤት ሲሰደድ”[በእርግጥ ተሰዷል ብዬ ለማመን ብቸገርም] አዲስ ጎጆ ሊሠራለት ዳድቶ፣ ወደሚድያ እንዲመጣ የመፈለጉ አንድምታ፣ አደገኛነቱ የቱም መንፈሳዊና ለእግዚአብሔርና ለሕዝቡ ቅድስና የሚቀና አገልጋይ ይጠፋዋል ብዬ አላስብም፡፡